በኢትዮ-ጅቡቲ መስመር ከ150 እስከ 250 ሺሕ የሚሆኑ ኢትዮጵያዊን በየዓመቱ እንደሚሰደዱ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ለአሐዱ አስታውቋል፡፡
እንደ ሀገር በተከሰተው የፖለቲካ ቀውስ፣ ስር የሰደደ ድህነት፣ ተመጣጣኝ የሆነ የገቢ ምንጭ አለማግኘትና በተያያዥ ችግሮች ዜጎች ሀገራቸውን ለቀው በመሰደድ ለተለያዩ የሰብዕዊ የመብት ጥሰቶች እየተጋለጡ መሆኑን፤ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር መከላከልና የተመላሽ ዜጎች ድጋፍና ክትትል መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ደረጄ ተግይበሉ ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
“የኢትዮጵያ የሕዝብ ቁጥር በየጊዜው እየጨመረ መሆኑ እንዲሁም፤ በገጠራማው ክፍል በቂ የሆነ የመሬት ሃብት አለመኖር ለችግሩ መባባስም እንደምክንያት የሚጠቀሱ ናቸው” ሲሉም መሪ ሥራ አስፈፃሚው ገልጸዋል፡፡
“ሕይወታቸውን ለመቀየር በሚል የቤተሰብ ጫና ተጨምሮበት ለስደት በሚዳረጉበትበት ወቅት፤ በሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ ምክንያቶች ሕይወታቸው የሚያልፍ ዜጎቻችን ቀላል አይደሉም” ሲሉም ተናግረዋል፡፡
መንግሥት በቀጣይ ለስደት አመቺ የሆኑ ድንበሮችን በጥብቅ ለመቆጣጠር ከጎረቤት ሀገራት ጋር በቅንጅት መስራቱን በማጠናከር እንዲሁም፤ ለዜጎች ደግሞ በቻለው መጠን በሀገራቸው ሰርተው የገቢ ምንጫቸውን የሚያሳድጉበትን የሥራ ዕድል ለመፍጠር እቅድ ይዞ እንደሚሰራ መሪ ሥራ አስፈፃሚው ገልጸዋል፡፡
ከ2014 እስከ 2017 ዓ.ም ብቻ ከ300 ሺሕ በላይ ኢትዮጵያዊን ከሳዉዲ አረቢያ፣ከሱዳን፣ከየመን ከቤሩትና መሰል ሀገራት ወደ ሀገራቸዉ መመለሳቸውን አሐዱ መዘገቡ ይታወሳል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
