በዱባይ ወንጀል ሠርተው በኢትዮጵያ የተሸሸጉ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ሥር በማዋል ምርመራ እየተካሄደ መሆኑን የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል አስታወቁ።
ኮሚሽነሩ ይህንን ያስታወቁት፤ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የዱባይ ፖሊስ የምርመራ ቡድን ጋር በወንጀል ምርመራ ዙሪያ በተወያዩበት ወቅት ነው።
በዱባይ ወንጀል ሠርተው በኢትዮጵያ ተሸሸገው የነበሩና በቁጥጥር ስር ውለው ምርምራ እየተካሄደባቸው ናቸው የተባሉት ተጠርጣሪዎችን ብዛትም ሆነ የወንጀል አይነት በተመለከተ ፌደራል ፖሊስ የገለጸው ነገር የለም።
በቀጣይ በሁለቱም ሀገራት ተፈላጊ የሆኑ ተጠርጣሪዎችን አሳልፎ በመስጠት በሕግ ተጠያቂ ለማድረግ በሚቻልበት ሁኔታም ላይ መወያየታቸውን ከፌደራል ፖሊስ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
