በ #ደቡብ_ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን ዳሰነች ወረዳ በዳሰነች ወረዳ 34 ቀበሌዎች ‘ሙሉ በሙሉ’ በኦሞ ወንዝ ሙላት መጥለቅለቃቸውና 81 ሺህ ሰዎች መፈናቀላቸውን ነዋሪዎች እና የመንግስት ኃላፊ ለአዲስ ስታንዳርድ ገለጹ።
“የኦሞራቴ ከተማ በውሃ ተከባለች፤ የጎርፍ መጥለቅለቁ ነገ ወይም ከነገ ወዲያ ከተማችን ሊገባ ይችላል፤ እጣፈንታችንን ቁጭ ብለን እየተጠባበቅን ነው” ሲሉ ስማቸውን እንዳይጠቀስ የጠየቁ በኦምራቴ ከተማ ነዋሪ ተናግረዋል።
ሌላኛው ስሜ ባይጠቀስ ያሉ እና በጎርፍ መጥለቅለቁ ምክንያት ተፈናቅለው ነበረሙስ በተባለ መጠለያ ተጠልለው የሚገኙ ነዋሪ በበኩላቸው፤ “የእርሻ ቦታዎችን ሁሉ ጠራርጓል። ቤቶችን አፍርሷል። ኦሞራቴ ከተማን ለመዋጥ ደግሞ አንድ ኪ.ሜ እንኳን አይሞላም የተቃረበው” ብለዋል።
ስማቸውም ሆነ የስራ ሀላፊነታቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የኦሞራቴ ከተማ የመንግስት ሀላፊ፤ የኦሞ ወንዝ ሞልቶ የቱርካና ሀይቅ ከኦሞራቴ ከተማ ከዚህ ቀደም ከነበረው 60 ኪ.ሜ ርቀት አሁን ላይ ወደ 1.3 ኪ.ሜ ርቀት ላይ መጠጋቱን ጠቅሰዋል።
