የኢትዮጵያ መንግሥት ባለፉት 5 ዓመታት ያወጣው ወጪ ከሚያገኘው ገቢ በከፍተኛ ደረጃ መብለጡን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር አስታውቋል።
የኢትየጵያ ኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር በዛሬው ዕለት 22ኛውን ዓለም አቀፍ ጉባዔ ያካሄደ ሲሆን፤ በመድረኩም ከወቅታዊ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበዋል።
በቀረበው ጥናትም የኢትዮጵያ መንግሥት ወጪው ከሚያገነው ከገቢ በከፍተኛ ደረጃ የበለጠ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በተቃራኒው መንግሥት ገቢው ከወጪው አንፃር አነስተኛ መሆኑን የገለጹት የማህበሩ ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር አረጋ ሹመቴ፤ በጥናቱ ‘የመንግሥት ወጪ አቅጣጫ ወዴት የሚያመዝን ነው?’ የሚለውም መጠናቱን ገልጸዋል፡፡
“በከፍተኛ ሁኔታ የመንግሥት ካፓታል ወጪ መቀነሱም በጥናቱ ተረጋግጧል” ብለዋል፡፡
“ከ2016 ዓ.ም በፊት የመንግሥት ወጪ ትልቁን መደበኛ በጀት እየያዘ ኢንቨስትመንት እየቀነሰ መሄዱ ማሳያ ነው” ያሉት ዶክተር አረጋ “መንግሥት ትልቁ ኢንቨስተር ቢሆንም የሚጠበቀውን ያህል ግን ኢንቨሰት እያደረገ ለካፒታል በጀትም እየተያዘ አይደለም” ሲሉ ጠቁመዋል።
ሌላው ትኩረት የተደረገበት ጥናት የመንግሥት ዕዳ ላይ የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ ዕዳ ከፍተኛ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በመድረኩም “ማንኛውም ሀገር ዕዳ አለበት” የተባለ ሲሆን፤ ዕዳው ከሀገር ውስጥም ሆነ ከውጪ ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል።
ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ዕዳ ያለበት የውጭ ዕዳ በመሆኑና ዕዳውም የመጣው በመንግሥት በራሱ እና የመንግሥት ተቋማት እንደ ኤልፓ፣ ቴሌኮም እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመሳሰሰሉ ተቋማት ናቸው ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ መልኩ ጥናቱ የኢትዮጵያ ዕዳ የመክፈል አቅሟም ለመመለከት የተሞከረ ሲሆን፤ ዕዳ የመክፈል አቅም የሚለካው ወደ ወጪ በሚላክ ምርት ጋር የተያያዘ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የኢትዮጰያ ዕዳ ከፍተኛው የውጭ ዕዳ በመሆኑ መለኪው ወደ ወጪ የሚላከው ምርቷ መሆኑ የተገለጸም ሲሆን፤ በዚህ አንፃር ሀገሪቱ ብዙ የውጭ ዕዳ አለባት ተብሏል፡፡ የሚካሄደዉ ጉባኤ እስከ ነገ የሚቀጥል መሆኑም ተገልጿል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
