ከወራት በፊት በከንቲባ አዳነች አቤቤ ተመርቆ ስራ የጀመረው ቤተ ሳይዳ አሜሪካን ሜዲካል ፕላዛ፣ የራሱን የሕክምና ኮሌጅ ለማቋቋም ማቀዱንና ዝግጅት እያደረገ መሆኑን በዛሬው ዕለት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቀ።
ተቋሙ በሰንጋ ተራ አካባቢ የሚገነባውን እና እስከ ጥር ወር የሚጠናቀቀውን ዘመናዊ የእናቶችና ሕፃናት እንዲሁም የመካንነት ሕክምና ማዕከልን ጨምሮ፣ በሁሉም የኢትዮጵያ ትልልቅ ከተሞች ቅርንጫፎችን የመክፈት ሰፊ ዕቅድ እንዳለው የዋና ስራ አስፈጻሚው ዶክተር አየለ ተሾመ ማብራሪያ ያመለክታል።
በመግለጫው ላይ በማኅበራዊ ሚዲያ የሚሰራጩ የዋጋ ተመን ቅሬታዎች “ሐሰት” መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን፣ የአገልግሎት ዋጋው መካከለኛ ገቢ ያለውን የኅብረተሰብ ክፍል ያማከለና በከተማው ካሉ ውድ ተቋማት አንጻር ሲታይ የሲሶ ያህል ቅናሽ ያለው መሆኑ ተገልጿል።
ተቋሙ ሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) የሚጠቀሙና በድምፅ የሚታዘዙ ዘመናዊ የሕክምና መሣሪያዎችን የታጠቀ ሲሆን፣ በአጠቃላይ 25 ሚሊዮን ዶላር (3.5 ቢሊዮን ብር) ወጪ እንደተደረገበት ታውቋል።
በሌላ በኩል፣ ዕውቋ ሞዴል ሃሴት ደረጀ የተቋሙ የመጀመሪያዋ የብራንድ አምባሳደር በመሆን የፊርማ ሥነ-ሥርዓት አካሂዳለች። ሞዴል ሃሴት በቀጣይ ከተቋሙ ጋር በመሆን በሴቶችና ሕፃናት ጤና፣ በተለይም በጡትና በማኅፀን በር ካንሰር ግንዛቤ ማስጨበጫ ዙሪያ በትኩረት እንደምትሠራ ገልጻለች።
ቤተ ሳይዳ አሁንም የአገልግሎት ጥራቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማስመዝገብና የካንሰር ማከሚያ ማዕከል ለማቋቋም ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋር በቅንጅት እየሠራ ይገኛል።
