የሀገር ውስጥ ባንኮች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በሚካሄዱት የውጭ ምንዛሬ ጨረታዎች ሂደትና ውጤት ላይ በቂ ግልጽነት አለመኖሩን በመተቸት ቅሬታቸውን እየገለጹ ናቸው።
ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የባንክ ባለሙያዎች ለካፒታል ጋዜጣ እንደተናገሩት፣ ባንኮች ለጨረታ ያቀረቡት ዋጋ ተቀባይነት ያገኘ ስለመሆኑ በግልጽ አይነገራቸውም። እንዲሁም የጨረታው ዝርዝር መረጃ ለሌሎች አካላት ሊጋራ ስለሚችልበት ሁኔታ ያላቸውን ስጋት አንፀባርቀዋል።
ሌሎች የባንክ ባለሙያዎች በበኩላቸው፣ ባንኮቻቸው ያቀረቡት ዋጋ ከአማካይ በታች ወይም በላይ በመሆኑ ብቻ ያለ በቂ ምክንያት ከጨረታው ውጪ እየተደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።
ማዕከላዊ ባንኩ የጨረታውን ውጤት ሲያሳውቅ ያሸነፉና የተሸነፉ ባንኮችን ዝርዝር እንዲሁም የተሳተፉ ባንኮችን ጠቅላላ ቁጥር በግልጽ እንደማያሳውቅ የዘርፉ ባለሞያዎች ተችተዋል።
በዚህም ምክንያት የባንክ ባለሙያዎቹ ማዕከላዊ ባንክ የጨረታ ሂደቱን የበለጠ ግልጽ እንዲያደርግና ሁሉንም ውጤቶች በዝርዝር እንዲያሳውቅ ጥሪ እያቀረቡ ይገኛሉ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ብሔራዊ ባንክ ከሐምሌ ወር ጀምሮ የውጭ ምንዛሬ ጨረታዎችን ሲያካሂድ የቆየ ሲሆን፣ በሚያዚያ 9 ቀን 2017 ዓ.ም. የተካሄደው የቅርብ ጊዜ ጨረታ አራተኛው ነው። በዚህ ዙር 26 ባንኮች በአማካይ በ131.495 ብር ለአንድ ዶላር ተመን 70 ሚሊዮን ዶላር ተከፋፍለዋል።
ባንኮቹ የጨረታ ስርዓቱ ፍትሃዊና አስተማማኝ እንዲሆን ግልጽነትን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።
Source: capitalethiopia
