የአሜሪካ ጦር በኢራን ስትራቴጂካዊ የወደብ ከተማ ባንደር አባስ የሚገኝ ወታደራዊ ስፍራን ዒላማ ያደረጉ የአየር ጥቃቶችን መፈጸሙን አስታወቀ።
የአሜሪካ ኃይሎች “በሆርሙዝ ወሽመጥ ዙሪያ ስጋት ደቅነው የነበሩ” አራት የኢራን ድሮኖችንም መትተው እንደጣሉ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ገልጿል።
እንደ ሴንትኮም ገለጻ ባንደር አባስ ውስጥ የሚገኘው ወታደራዊ ስፍራ ጥቃት የተፈጸመበት አምስተኛውን ድሮን ለመተኮስ ሲዘጋጅ ነው። የኢራን መገናኛ ብዙኃን ከከተማው በስተምስራቅ አቅጣጫ የፍንዳታ ድምፆች መሰማታቸውን ዘግበዋል።
ጥቃቱ የተፈጸመው በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰው ጠንካራ ያልሆነ ተኩስ አቁም ተግባራዊ መሆን ባላቆመበት ነው።
በሆርሙዝ ወሽመጥ ለሚደረግ የመርከብ ጉዞ መቆም እንዲሁም የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መናር ምክንያት የሆነውን ይህንን ሦስት ወር የሞላው ጦርነት ለማቆም የሚደረጉ ረጅም ድርድሮች እስካሁን መፍትሔ አላስገኙም።
አሜሪካ ራሷን ለመከላከል እንደሆነ በመግለጽ ኢራን ውስጥ ባሉ ዒላማዎች ላይ ጥቃት ስትፈጽም ይህ በሦስት ቀናት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። እንደአዲስ ጥቃቶች መድረሳቸው የተኩስ አቁም ስምምነቱን አደጋ ላይ ጥሎታል።
ሴንትኮም የተወሰደውን ወታደራዊ እርምጃ “የተመጠነ፣ በግልጽ ራስን የመከላከል የሆነ እንዲሁም የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለማስቀጠል ያለመ” ሲል ገልጾታል።
አሜሪካ ሰኞ ዕለት ደቡባዊ ኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የኢራንን የሚሳኤል ጣቢያዎች እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ፈንጂ ለማጥመድ የሞከሩ መርከቦች ዒላማ እንደተደረጉ ተገልጿል። ሴንትኮም እነዚህ ጥቃቶች የተወሰዱት “ወታደሮቻችንን ከኢራን ኃይሎች ከሚመጡ ስጋቶች ለመጠበቅ” ነው ብለዋል።
ጥቃቶቹን “ትልቅ የተሰስ አቁም ጥሰት” ስትል ያወገዘችው ኢራን፤ “የትኛውም ጠበኛ ድርጊት ምላሽ ሳይሰጠው እንደማያልፍ” ዝታለች።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማክሰኞ ዕለት የአሜሪካ ድሮንን መትቶ መጣሉን እንዲሁም ወደ ኢራን የአየር ክለል የገቡ ተዋጊ ጄት እና ድረኖን ላይ ተኩስ መክፈቱን ገልጿል። እነዚህ እርምጃዎች የተወሰዱት መቼ እንደነበር ግን አልተጠቀሰም።
ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው ትናንት በተካሄደ የካቢኔ ስብሰባ ላይ፤ ኢራን “በንዴት እየተደራደረች ነው” ሲሉ ተደምጠዋል። አክለውም በመጪው ህዳር የሚካሄደው የአጋማሽ ጊዜ የሥልጣን ዘመን ምርጫ የጦርነት ስትራቴጂያቸው ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድር ተናግረዋል።
