የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በአርሲ ዞን በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች የተከሰተውን የንጹሃን ግድያና የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎ በጽኑ ያወግዛል፡፡
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አመራሮች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በአርሲ ዞን (በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች) በቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዬች እና ምዕመናን ላይ አሰቃቂ ግድያ መፈጸሙን እና አብያተ ክርስቲያናትን የማውደም ተግባር መካሄዱን በመጥቀስ ያወጣችውን የሀዘን መግለጫ የተመለከትነው በታላቅ ልብ ስብራት እና ጥልቅ ሀዘን ነው፡፡
ከዚህም በመነሳት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሃይማኖት አባቶች፣ ካህናት እና ምዕምናን ከሁሉም በላይ ጉዳት ለደረሰባቸው ቤተሰቦች፣ ዘመዶች፣ ወዳጆች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ፈጣሪ መጽናናቱን እና ጽናቱን እንዲሰጣችሁ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ከልብ ይመኛል፡፡
ቀደም ሲል አሁን ችግር በተከሰተባቸው አካባቢዎች ተመሳሳይ ጥቃት እንዳይፈጸም መንግሥት ለንጹሃን ዜጎቻችን አስተማማኝ ጥበቃና ከለላ እንዲያደርግ ጉባኤችን መጠየቁ የሚታወስ ነው፡፡ ሆኖም ችግሩ ሳይቀረፍ ተጨማሪ ጉዳትና ስቃይ በነዚሁ ቦታዎች በድጋሜ መከሰቱ ሀዘናችንን እጥፍ ድርብ አድርጎታል፡፡
ይህ በንጹሃን ዜጎቻችን ላይ የሚፈጸመው ግድያ እና ስቃይ ከፈጣሪ እይታና ፍርድ የተሰወረ ባይሆንም መንግሥት የዜጎችን ሰላምና ደህንነት የማረጋገጥ ተቀዳሚ ኃላፊነቱን አሁንም እንዲወጣ እየጠየቅን በተለይም በአሁኑ ወቅት ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ዜጎች እንዲሁም በአካባቢው ለሚኖሩ የጥቃት ስጋት ላለባቸው ወገኖቻችን አስተማማኝ ጥበቃ እንዲያደርግ የአደራ ጥሪያችንን በድጋሜ እናቀርባልን፡፡
በተያያዘም ይህን አሰቃቂ ወንጀል የፈጸሙትን አካላት መንግሥት በአፋጣኝ ተከታትሎ ለፍርድ እንዲያቀርብና ሂደቱንም ለሕዝብ እንዲያሳውቅ ጥያቄ እናቀርባለን፡፡
አባል የሃይማኖት ተቋማት ይህን አሰቃቂ ወንጀል እና አጸያፊ ሀጢያት በአንድነት እንዲያወግዙ መልዕክት እናስተላልፋለን፡፡
እንዲሁም የአካባቢው ማህበረሰቦች ይህ ክፉ ቀን የሚያልፍ መሆኑን አወቃችሁ በአንድነት፣ በመተባበር እና በመተጋገዝ ተጨማሪ ጉዳት እንዳይከሰት የአቅማችሁን ያክል ትብብር እና ድጋፍ ታደርጉ ዘንድ በታላቅ አክብሮት የአደራ ጥሪ እናቀርባለን፡፡
ፈጣሪ ኢትዮጵያን እና ሕዝቦችዋን ይጠብቅ ይባርክ
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ
