የቱሪዝም ሚኒስቴር ባካሄደው የሆቴሎች ምዘና በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚገኙ 15 ሆቴሎች የኮከብ ደረጃቸውን ተነጥቀዋል። ከእነዚህ ውስጥ አንዳንዶቹ ከአንድ ዓመት በላይ አገልግሎት መስጠት ያቆሙ ወይም የአገልግሎት ዘርፋቸውን የቀየሩ መሆናቸውን ተሰምቷል።
ዲሚትሪ፣ ሲዮናት፣ ክራውን፣ አምባሳደር፣ ፓራማውንት፣ በሻሌ፣ ሐራምቤ፣ አስትራ ሆቴሎች አገልግሎት መስጠት ካቆሙ በኋላ የኮከብ ደረጃቸው የተነጠቀ ሲሆን፣ ሞዛይክ፣ ናርዳን፣ ሊ ማስተር ሆቴሎች የአገልግሎት ዘርፋቸውን በመቀየራቸው ደረጃቸው ተነስቷል።
በተጨማሪም ዋቢ ሸበሌ እና ደሳለኝ ሆቴሎች ለምዘናው ተባባሪ ባለመሆናቸው፣ እንዲሁም ሲያቲን ሆቴል የስያሜና የባለቤትነት ለውጥ በማድረጉ የኮከብ ደረጃቸውን አጥተዋል።
በ2017 ዓ.ም. በ92 ሆቴሎች ላይ በተደረገው ዳግም ምዘና፣ ከውጭ ገጽታ ጀምሮ በ12 መስፈርቶች ላይ ተመርኩዞ የ40 ሆቴሎች ደረጃ ይፋ ሆኗል። ከእነዚህ 40 ሆቴሎች ውስጥ 11 ሆቴሎች ባለ አምስት ኮከብ ደረጃን ያገኙ ሲሆን፣ 34ቱ ዳግም ምዘና የተደረገላቸው ሲሆን፣ ስድስት አዳዲስ ሆቴሎች ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኮከብ ደረጃ ገብተዋል።
Source: capitalethiopia
