የዝነኛው ፎቶ መነሻ 43 ዓመታትን ወደኋላ ይወስደናል። በ1975 ዓ.ም ማለት ነው። ቦታው ደግሞ በቀድሞ አጠራር አርሲ ክፍለ ሀገር ልዩ ስሙ ጎቤ ቀበሌ። የወቅቱ ፕሬዚዳንት መንግስቱ ኃይለማሪያም ባሌ ሁለገብ የገበሬዎች ማሰልጠኛን ለለመመረቅ ከስፍራው ተገኝተዋል።
በወቅቱ በባህላዊ ጭፈራ ልዩ አቀባበል ከሚያደርጉ ወጣቶች መካከል፤ የአርሲ ክፍለ ሀገር የኪነት ቡድን አባል የነበረችው ደነቤ ደዎ አንዷ ነበረች።
በባህላዊ ጭፈራው ማሸብሸብ ላይ በነበረቸው ወጣት የተመሰጠው ፎቶ አንሺ የደነቤን ምስል በካሜራ አስቀረው።
በእርግጥ በዚህ መልኩ እንደዋዛ የተነሳው ፎት ለዓመታት የሀገር ገፅታ ማስተዋወቂያ ይሆናል ብሎ የጠበቀ አልነበረም። ይሁንና ሳይጠበቅ የወጣቷ ምስል ከኢትዮጵያ አልፎ ዓለም ላይ ታወቀ።
የቀድሞ ኢትዮጵያ ቱሪዝም ኮሚሽን “የአርሲዋ ቆንጆ” በሚል ኢትዮጵያን በመላው ዓለም አስተዋወቀበት።
ሰሞኑን የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽን ባዘጋጀው መድረክ ላይ ከጋዜጠኛ የእናትፋንታ ዉቤ ጋር የተገኙት የያኔዋ ወጣት ወ/ሮ ደነቤ፤ ፎቶውን ከዛሬ ከ43 ዓመት በፊት ‹‹ወንደቤ›› በተሰኘ የአርሲ አካባቢ ባህላዊ አልባስ ሳያስቡት መነሳታቸውን ይገልጻሉ።
“ፎቶው ከተበተነ በኋላ በትውልድ አካባቢዬ ምን ገጥሟት ነው በሚል ቤተሰብ ግራ ተጋብቶ ነበር” የሚሉት ወ/ሮ ደነቤ፤ ላለፉት አራት አስርት ዓመታት ፖስተሩ ዝነኛ ቢሆንም እርሳቸው ግን ምንም እውቅና እንዳላገኙ ይገልጻሉ።
“ፖስተሩ ላይ ያለችው ወጣት እኔ ስለመሆኔ ማንም አያውቀኝም” የሚሉት ወ/ሮ ደነቤ፤ እኔ በባህሌ እኮራለሁ፣ ባህሌንም በማስተዋወቄ ደስታ ይሰማኛል፤ ነገር ግን የፎቶዬን ያህል አለመታወቄ ቅር ያሰኘኛል ይላሉ።
የኢሬቻ በዓል በወጣትነታቸው ላይ ብዙ ትዝታ አለው። በጭፈራም ይሳተፉ ነበር። በተለይም በወጣትነታቸው በነበሩበት የአርሲ ክፍለ ሀገር የኪነት ቡድን ውስጥ አርሲ አካባቢ በስፋት የሚታወቀውን “ትሪ” የጭፈራ ስልት በማስተዋወቅ በስፋት ሠርተዋል።
EBC
