በምግብ ዋስትና እና በሥነ-ምህዳር መቋቋም ፕሮግራሞች ላይ ከአስር አመታት በላይ ልምድ ያካበቱት ኢትዮጵያዊው አቶ እዛና ካሳ፣ በኡጋንዳ የተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ተወካይ ሆነው ተሾሙ።
የኡጋንዳ መንግስት ይሁንታውን የሰጠበት ይህ ሹመት በድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ኩ ዶንግዩ የተከናወነ ሲሆን፣ አቶ እዛና አንቶኒዮ ኩዌሪዶን በመተካት ስራቸውን ይጀምራሉ።
ሹመቱ ድርጅቱ በአቶ እዛና ሰፊ የመስክ ልምድ እና በአፍሪካ ቀንድ ባሉ ውስብስብ አካባቢዎች በነበራቸው ውጤታማ የስራ አፈጻጸም ላይ ያለውን ጥልቅ እምነት የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል።
አቶ እዛና ካሳ ወደ ፋኦ የተቀላቀሉት እ.ኤ.አ. በ2015 በደቡብ ሱዳን የፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ በመሆን ሲሆን፣ ከዚያም በሶማሊያ የድንገተኛ አደጋ አስተባባሪና የከፍተኛ ፕሮግራም መኮንን በመሆን በሰብአዊ እርዳታና በልማት ስራዎች ላይ ስትራቴጂካዊ አመራር ሰጥተዋል።
ድርጅቱን ከመቀላቀላቸው በፊትም እንደ ‘አክሽን አፍሪካ ሄልፕ ኢንተርናሽናል’ ባሉ ታዋቂ አለም አቀፍ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ በዳይሬክተርነት ደረጃ ሰርተዋል።
በትምህርት ዝግጅታቸውም ከሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በግብርና የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን፣ ከለንደን ዩኒቨርሲቲ በዘላቂ ግብርና እና ገጠር ልማት የማስተርስ ዲግሪያቸውን እንዲሁም ከዩናይትድ ስቴትስ ኢንተርናሽናል ዩኒቨርሲቲ (ናይሮቢ) የኤግዚኪዩቲቭ ኤምቢኤ አግኝተዋል።
አቶ እዛና በሹመታቸው ወቅት ባስተላለፉት መልእክት፣ “የአፍሪካ ዕንቁ” በመባል የምትታወቀው ኡጋንዳ በአካባቢው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ያላትን እምቅ አቅም አድንቀዋል።
ከኡጋንዳ መንግስትና ከገጠር ማህበረሰቦች ጋር በመተባበር ዘላቂና ሁሉን አቀፍ የግብርና ስርዓትን ለመገንባት ቁርጠኛ መሆናቸውንም ገልጸዋል። ፋኦ ከኡጋንዳ ጋር ያለውን የቆየ አጋርነት በማጠናከር፣ በምርታማነት መጨመርና በገጠር ኢኮኖሚ ግንባታ ላይ ትኩረት አድርገው እንደሚሰሩም ይጠበቃል።
