በኢትዮጵያ የአካል ብቃት ስልጠና ዘርፍ ስመ-ጥር የሆነው ኢንስትራክተር ዳዊት መኮንን፣ “አካል በብቃት” የተሰኘ ሦስተኛ መጽሐፉን ዓርብ መጋቢት 25 2018 ዓ.ም በይፋ አስመርቋል።
መጽሐፉ ሳይንሳዊ የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎችን ከሥነ-ምግብ መመሪያዎች ጋር በማጣመር፣ በተለይም በሥራ ጫና ምክንያት ወደ ስፖርት ማዕከላት መሄድ ለማይችሉ ግለሰቦች እንደ መመሪያ ሆኖ እንዲያገለግል ተደርጎ የተዘጋጀ ነው።
ኢንስትራክተር ዳዊት ከዚህ ቀደም ካሳተሟቸው “የስፖርት ማሽን አጠቃቀም” እና “ስፖርት ያለ መሳሪያ” መጽሐፍት ቀጥሎ የቀረበው ይህ አዲስ ሥራ፣ ማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል ባሉበት ቦታና በተመቻቸው ስፍራ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ የሚያስችሉ ዝርዝር ትንታኔዎችን አካቷል።
መጽሐፉ ስፖርትን ለመሥራት “ጊዜ የለኝም” ለሚሉ የከተማ ነዋሪዎች እንደ ዋነኛ መፍትሔ የቀረበ ሲሆን፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለጥቂቶች ሳይሆን ለሁሉም የጤና ዋስትና መሆኑን ለማስገንዘብ ያለመ ነው።
ለታሪክ አድቨርታይዚንግ እና ህትመት ወደ ንባብ ያመጣው ይህ መጽሐፍ፣ በ11 ምዕራፎች የተከፋፈለና 250 ገፆችን የያዘ ሲሆን በ1,199 ብር ለገበያ ቀርቧል።
በመጽሐፉ ውስጥ የሕፃናት የአካል ብቃት፣ የባህላዊ ጭፈራ ከስፖርት ጋር ያለው ሳይንሳዊ ትስስር፣ እንዲሁም በተለያዩ ዘርፎች ያሉ ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች ተሞክሮ ተካቶበታል።
ኢንስትራክተር ዳዊት መኮንን በመጽሐፍ ዝግጅትና በሚዲያ አማራጮች የአካል ብቃትን ባህል ለማድረግ የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ታውቋል።
