ታሪካዊው ኢትዮጵያ ሆቴል ሙሉ በሙሉ ሊፈርስ እንደሆነ ፎርቹን ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ እንደዘገባው በአሁኑ ወቅት ከሆቴሉ ጀርባ የሚገኙት ቦታዎችና ግንባታዎች በመፍረስ ላይ ሲሆኑ ሆቴሉ እስከሚቀጥለው ጥቅምት ፈርሶ የሚጠናቀቅ ይሆናል ተብሏል።
ይህ ሆቴል የሚፈርሰው በምትኩ ሰማይ ጠቀስ ፎቅ ሊሰራበት ነው፡፡ የሆቴሉ ባለቤት የሆነው ቢኬ ግሩፕ ከመንግስት ከገዛው በኋላ የማስፋፊያ ስራ ወዲያውኑ የጀመረ ሲሆን ከይዞታው 4000 ካሬ ሜትር በተጨማሪ በ5500 ካሬ ሜትር ላይ ትልቅ ህንፃ የመገንባት እቅድ እንዳለው አስታውቆ ነበር፡፡
ከመነሻው እቅዱ ባለ63 ፎቅ ህንፃ የመገንባት ቢሆንም በአካባቢው ካሉት ትልልቅ ህንፃዎች አኳያ ፕላኑን ለማሻሻል ውሳኔ ላይ ቢደርስም የተሻሻለውን እቅድ ግን ገና ይፋ አላደረገም፡፡
እንደዘገባው ባለ 5 ህንፃ የሆነው ኢትዮጵያ ሆቴል በአሁኑ ወቅት 109 ክፍሎች ያሉትና በ3 ፈረቃ የሚሰሩ 140 ሰራተኞች ያሉት ነው፡፡ የሆቴሉ አስተዳደር ከሳምንታት በፊት ሰራተኞቹን ሰብስቦ ሆቴሉ በቅርቡ እንደሚፈርስ የነገራቸው ሲሆን እስከዛው ግን ስራቸውን እንዲቀጥሉ ገልፆላቸዋል፡፡
አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ ሰራተኛ እንደተናገረው ሆቴሉ ከፈረሰ በኋላ የሰራተኛ ቅነሳ እንደማይኖር ቃል ተገብቶላቸዋል፡፡
