ኢትዮጵያ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ የሰጠቻቸውን የቃል ማረጋገጫዎች በጽሑፍ ስምምነት እንድትደግፍ ግብፅ ጠየቀች። ይህ ጥያቄ የመጣው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ግድቡ በመስከረም ወር እንደሚመረቅ ከገለጹ በኋላ ነው።
የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ሙስጠፋ ማድቡሊ፣ በቅርቡ ብራዚል ውስጥ በተካሄደው የብሪክስ ስብሰባ ጎን ለጎን ከአብይ አህመድ ጋር መነጋገራቸውን ጠቁመዋል።
በብሪክስ ስብሰባ ወቅት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ግድቡን “ግብፅንና ሱዳንን ሳይጎዳ” የማጠናቀቅ እና ትብብርን የመቀጠል ፍላጎታቸውን ገልጸው ነበር። ይሁን እንጂ ማድቡሊ፣ እነዚህ የቃል ማረጋገጫዎች በሁለቱ ሀገራት ወይም በናይል ተፋሰስ ሀገራት መካከል ያለውን የወደፊት ግንኙነት በሚያደራጅ የጽሑፍ ሰነድ ውስጥ መተርጎም አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ “የግብፅ አቋም በፍጹም አልተለወጠም፤ በአባይ ውሃ ድርሻዋ ላይ ምንም አይነት ጉዳት እንዲደርስ አትፈቅድም” ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል። ግብፅ የልማት ተቃዋሚ ባትሆንም፣ በአባይ ውሃ ላይ ያላትን ህጋዊ መብት እንደምትጠብቅም አስረድተዋል።
የህዳሴ ግድብን በተመለከተ ኢትዮጵያና ግብፅ ለረጅም ጊዜ የዘለቀ አለመግባባት ያለባቸው ሲሆን፣ ግድቡን ስለመሙላትና ስለማስኬድ ስምምነት ላይ እስካሁን አልደረሱም።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ለህዝብ ተወካዮች ምክርቤት በሰጡት ማብራሪያ ፤ ግድቡ በመስከረም ወር እንደሚመረቅ እና፣ ፕሮጀክቱ ለቀጠናው ትብብር “ዕድል” እንጂ “አደጋ” እንደማይሆን በመጥቀስ ከግብፅ ጋር ውይይት ለመቀጠል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
በ እኤአ በ 2011 የተጀመረውን የህዳሴ ግድቡን በሚመለከት በተደጋጋሚ በአፍሪካ ህብረት እና በአለም አቀፍ ሽምግልና የተደረጉ ድርድሮች ቢኖሩም፣ ሦስቱ ተፋሰስ ሀገራት (ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብፅ) የረጅም ጊዜ የውሃ አያያዝ ላይ ህጋዊ አስገዳጅ ስምምነት መድረስ አልቻሉም።
CapitalNews
