ኢትዮጵያ ያነሳችው የባሕር በር ጥያቄ ትክክለኛ እና ወቅቱን የጠበቀ መሆኑን የታሪክ ምሁራን ገለጹ።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ በሰላማዊ እና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ መፈታት ይኖርበታልም ነው ያሉት የታሪክ ምሁራኑ ከኢትዮጵያ ሬዲዮ ጋር በነበራቸው ቆይታ።
የታሪክ ምሁሩ ተመስገን ንጉስ (ዶ/ር) በሰላማዊ እና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ጥያቄዎች መነሳታቸውን አስታውሰው፤ እነዚህ ጥያቄዎች በሰላማዊ መንገድ መፈታት አለባቸውም ብለዋል።
ኢትዮጵያ በቀይ ባሕር ላይ የመጠቀም ሙሉ መብት እንዳላት እና ዓለምአቀፍ ሕጎች ጭምር ይህን እንደሚደግፉም አንስተዋል።
ከጥንት የኢትዮጵያውያን የስልጣኔ ዘመን ብንነሳ እንኳን እቃን በ እቃ በመለዋወጥ የጀመረው የንግድ ሥርዓት ላይ የባሕር በር ወሳኝ ሚና እንደነበረው አስታውሰዋል።
በቀይ ባሕር ቀጠና ላይ እየጨመረ በመጣው የጂኦ ፖለቲክስ የበላይነት እና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ላይ ኢትዮጵያ ሚና ሊኖራት ይገባል ያሉት አምባሳደር ግሩም አባይ፥ የተነሳው ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ ሁሉም ኢትዮጵያውያን በአንድነት የሚቆሙበት ጊዜ አሁን ነው ብለዋል።
የገቢ እና ወጪ ንግዶችን በራሳችን የባሕር በር እናከናውን ነበር አሁን ደግሞ ባለን የሕዝብ ቁጥር መጨመር እና በወጪ ንግዱ መጨመር ምክንያት የባሕር በር የሚያስፈልገን ወሳኙ ሰዓት ላይ ተገኝተናልም ነው ያሉት ምሁራኑ።
