ኤስ ኦ ኤስ የህጻናት መንደሮች በኢትዮጵያ አርቲስት አለማየሁ ታደሰን በድርጅቱ ታሪክ የመጀመሪያው የብራንድ አምባሳደር አድርጎ መሰየሙን አስታውቋል፡፡
ይህም ድርጅቱ የማህበረሰብ ተሳትፎን ለማጎልበት እና በመላው ኢትዮጵያ ያሉ ህጻናትን እና ወጣቶችን የመጠበቅ እና የማብቃት ተልዕኮውን ለማጎልበት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን የተናገሩት በኤስኦኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ እና ደቡብ ሱዳን ብሔራዊ ዳይሬክተር አቶ ሣህለማርያም አበበ ናቸው ፡፡
ድርጅቱ ብራንድ አምባሳደር ለመሰየም የወሰነው ፕሮግራሞቹን እያሰፋ ባለበትና የሀገር ውስጥ ሃብት የማሰባሰብ ጥረቱን እያጠናከረ ባለበት ወቅት ነው። ይህም ለብዙ ማህበረሰቦችን ለመድረስ፣ ሰፊ ተሳትፎን ለማነሳሳት እና ዘላቂነት ያለው ድጋፍን ለማረጋገጥ በማለም ነው ብለዋል፡፡
ኤስኦኤስ የህጻናት መንደሮች በኢትዮጵያ ተልዕኮውን የሚያጎላ፣ የህጻናትን መብት የሚያስከብር እና በአገር ውስጥ የሚገኙት ባለ ድርሻ አካላት መካከል መተማመንን ለማጠናከር የሚረዳ በጎ ተጽእኖ ፈጣሪ አካል ስለሚያስገልግ ነው ሲሉ ገልፀዋል።
የብራንድ አምባሳደሩ ሚናም ድርጅታዊ አጋርነትን ለማስፋት፣ የገንዘብ ማሰባሰብ ጥረቶችን ለማጎልበት እና በቂ የወላጅ እንክብካቤ ሳያገኙ የሚያድጉ ህጻናት እና ወጣቶች የበለጠ የህዝብ ትኩረት እንዲያገኙ ለማስቻል ያለመ ነው።
የአርቲስት አለማየሁ ታደሰ ምርጫ በጥንቃቄ እና ግልፅ አሰራርን የተከተለ ሲሆን ይህም የእጩነት ምዕራፍ፣ የአስመራጭ ኮሚቴ ዝርዝር ግምገማ እና ሰፊ የሰራተኞች ተሳትፎን ያካተተ እንደነበር ገልፀዋል።
አርቲስት አለማየሁ ታደሰም ከኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች “የብራንድ አምባሳደር መሆን ከማዕረግ በላይ የሆነ እና ትክክለኛ ትርጉም ያለው አስተዋጽኦ ለማበርከት የሚያበቃ ትልቅ ሃላፊነት እና እድል መሆኑን ተናግሯል ።
