በሴቶች የአውሮፓ ዋንጫ ፍጻሜ እንግሊዝ ስፔንን በመለያ ምት በማሸነፍ ሻምፒዮን ሆናለች።
አንድ ሰዓት ላይ በባዝል በተደረገው የፍጻሜ ጨዋታ ሁለቱ ቡድኖች የተገናኙበት መደበኛ 90 ደቂቃ አንድ አቻ ተጠናቋል።ለሁለቱም ቡድኖች የአርሰናል ተጫዋቾች ግቦቹን አስቆጥረዋል።
34ሺህ ተመልካቾች በታደሙበት ሴንት ጃኮብ ፓርክ ስቴዲየም ማሪዮና ካልዴንቲ ለስፔን እና አሊሲያ ሩሶ ለእንግሊዝ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው።
አሸናፊውን ለመለየት በተጨመረው 30 ደቂቃ ግብ ባለመቆጠሩ ቡድኖቹ ወደ መለያ ምት አምርተዋል።
በተሰጠው መለያ ምትም እንግሊዝ 3 ለ 1 አሸንፋለች። የ2022 የአውሮፓ ዋንጫ አሸናፊዋ እንግሊዝ በተከታታይ ለ2ኛ ጊዜ የአህጉሩ ሻምፒዮን ሆናለች።
በሲውዘርላንድ አስተናጋጅነት ሲካሄድ በቆየው ድግስ የአውሮፓ ዋንጫን አንስታ የማታውቀው የዓለም ሻምፒዮኗ ስፔን፤ ከዚህ ክብር ጋር ለመጀመርያጊዜ የምትገናኝበትን አጋጣሚ ሳትጠቀምበት ቀርታለች።
ሁለቱ ሀገራት በ2023 በተገናኙበት የዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ስፔን 1 ለ0 አሸንፋ ዋንጫውን ማንሳቷም ይታወሳል።
