ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተወዳዳሪነታቸውንና ተመራጭነታቸውን ማሳደግ እንዳለባቸው የትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አስገነዘቡ።
የትምህርት ሚኒሰትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲዎች በተማሪዎች ተመራጭና ተወዳዳሪ ለመሆን መስራት ይኖርባቸዋል።
በአካባቢያቸው የሚገኙ የማዕድን፣ ቱሪዝምና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች ላይ ትኩረት አድርገው የትምህርት ፕሮግራማቸውን ለይተው ተወዳዳሪ ሊሆኑ እንደሚገባም ተናግረዋል።
በ2018 የትምህርት ዘመን የዩኒቨርሲቲዎችን ብቃት በትክክል መለየት የሚቻልበት እውቅና የመስጠት ስራ ይጀመራል ብለዋል።
የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት ኮራ ጡሹኔ፤ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥና የዘርፉን ችግሮች ለመፍታት በተከናወኑ ተግባራት ለውጦች እየተገኙ መሆኑን ገልጸዋል።
ሆኖም የትምህርት ጥራት ጉዳይ የባለድርሻ አካላትን ርብርብ እንደሚጠይቅና ቀሪ በርካታ ስራዎች ማከናወን እንደሚገባ ተናግረዋል።
የሪፎርም ስራዎቹ በተለያዩ ጉዳዮችና ኢንሼቲቮች ተዋቅረው በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ተግባራዊ እንደሚደረጉ ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የቁልፍ ተግባራት አፈጻጸም ፊርማ ስነ-ስርዓት ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጂጌ(ዶ/ር)፣ የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች፣ የዩኒቨርሲቲዎች የቦርድ አመራር አባላትና የዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንቶች ተገኝተዋል ሲል የዘገበው ኢዜአ ነው።
