ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ኬንያን ከሦስተኛ አለም ወደ አንደኛ አለም ለማሸጋገር የ30 አመት ታላቅ እቅድ እንዳላቸው አስታውቀዋል።
ሩቶ የረዥም ጊዜ ራዕያቸውን አስመልክተው ሲናገሩ፤ ኬንያ በትኩረት በማቀድና ተከታታይ ትግበራ በማድረግ፣ ፈጣን እድገት ያስመዘገቡት እንደ ደቡብ ኮሪያ፣ ሲንጋፖርና ቻይና ያሉ ሀገራትን አርአያ ትከተላለች ብለዋል፡፡
“ኬንያን ከሦስተኛ ዓለም ወደ አንደኛ ዓለም አገር ለማሳደግ 30 ዓመታትን ይወስድብናል – ልክ እንደ ኮሪያ፣ ሲንጋፖርና ቻይና። በ2055 ይህች ሀገር የአንደኛ ዓለም ሀገር ትሆናለች” ሲሉ በልበ ሙሉነት ተናግረዋል።
ፕሬዚዳንቱ አስተዳደራቸው በመሰረተ ልማት ዝርጋታ፣ በኢንዱስትሪ ማስፋፋት፣ በትምህርት ማሻሻያና በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን መሰረት እየጣለ መሆኑን አፅንዖት ሰጥተዋል – እኒህም በሚቀጥሉት አስርት አመታት ኬንያን የአለም ግዙፍ ኢኮኖሚ ያደርጋታል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡
