ባንኩ ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው ቀነ ገደብ አስቀድሞ የተከፈለ ካፒታሉን 5 ቢሊዮን ብር እንዳደረሰም ጠቅሷል።
ባንኩ ይህንን ያስረዳው ባካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ባወጣው ሪፖርት ነው።
ዘምዘም ባንክ በ2017 በጀት ዓመት አሳካሁት ያለው 1.23 ቢሊዮን ብር ትርፍ በባንኩ ታሪክ ከፍተኛው ነው ብሏል፡፡
ይህም የመጀመሪያውን የትርፍ ክፍፍል ለመስጠት የሚችልበት ደረጃ ላይ ነው ሲልም ጠቅሷል፡፡
የባንኩ አጠቃላይ ሀብት በበጀት ዓመቱ መጨረሻ 16.6 ቢሊዮን ብር ደርሷል ይህም ከቀዳሚው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር 39 ከመቶ እድገት ማሳየቱ ተነግሯል።
የተቀማጭ ገንዘቡ ከ2016 በጀት ዓመት የ69 ከመቶ ጭማሪ በማሳየት 11.6 ቢሊዮን ብር መድረሱም በሪፖርቱ ሰፍሯል።
ባንኩ አዳዲስ የቦርድ አባላት ምርጫ አካሂዷል።
የዘምዘም በንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ ናስር ዲኖ(ዶ/ር) “ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተቋማት እንዲያሟሉ የደነገገውን የ5 ቢሊዮን ብር ካፒታል ገደብ ከቀነ ገደቡ አስቀድመን ማሟላት ብቻ ሳይሆን፣ ባንካችን ለባለአክሲዮኖቹ የትርፍ ክፍፍል ማከፋፈል ወደ የሚጀምርበት ታሪካዊ ምዕራፍ ተሸጋግረናል” ብለዋል፡፡
የባንኩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ መሊካ በድሪ በበኩላቸው፣ የተገኘው ውጤት ባንኩ በስትራቴጂያዊ መንገድ በቴክኖሎጂ ላይ ያደረገው ኢንቨስትመንት ውጤት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ዘምዘም ባንክ በአዲስ አበባ ለሚገነባው ዋና መስሪያ ቤት ሀንፃ የዲዛይን ስራ እና የአማካሪ መረጣ መጠናቀቁን ተነግሯል፡፡
