የሲውዲን ነዳጅ አጓጓዥ ኩባንያ የሆነው ‘ስቴና በልክ’ ዋና ስራ አስፈጻሚ በአሁኑ ሰዓት የኩባንያው መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉበት “ምንም ዕድል” እንደሌለ ተናገሩ።
የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኤሪክ ሃኔል ከቢቢሲ ሬዲዮ 4 ‘ቱዴይ’ ፕሮግራም ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ “ይህንን አይነት እርምጃ ከመውሰዳችን በፊት” በውሃ መስመሩ በኩል በሰላም ለማለፍ “ከሁለቱም፤ ከኢራን እና አሜሪካ የደኅንነት ዋስትና ያስፈልገናል” ብለዋል።
የንግድ መርከቦች በድጋሚ ጉዞ እንዲጀምሩ የሚያስችለው አስፈላጊ ሁኔታ ሊፈጠር የሚችለው የሰላም ስምምነት ሲፈረም ብቻ መሆኑን ገልጸዋል።
“ከጥቂት ሳምንታት በፊት፣ እስከ ባለፈው ሳምንት ድረስ ባለው ጊዜ በአንድ ሳምንት ገደማ ውስጥ እንድናልፍ የሚያደርግ አንድ ነገር ይፈጠራል የሚል ተስፋ ነበረን” ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ አሁን ግን ሁኔታው “የተቆለፈ” ሆኗል ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።
