!
ከተገነባ 64 ዓመታትን ያስቆጠረውና በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ምዕመናን የሚሳለሙት የታሪካዊው የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሕንጻ ቤተክርስቲያን፣ በአሁኑ ወቅት ሰፊ የዕድሳት ሥራ እየተከናወነለት ይገኛል።
ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት በተሰጠ መግለጫ፣ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስና ሌሎች ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት የሕንጻውን ጥንታዊ ይዘት ለመጠበቅና የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል የጥገና ሥራ መጀመሩ ይፋ ሆኗል።
የዕድሳቱ ዋና ዓላማ በጊዜ ብዛትና በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በቤተክርስቲያኑ ጣሪያና ግድግዳ ላይ የደረሱ ጉዳቶችን በባለሙያዎች የታገዘ ጥገና በማድረግ የታሪካዊ ቅርሱን ዕድሜ ማራዘም ነው።
ፕሮጀክቱ የመቅደሱን፣ የቅኔ ማሕሌቱንና የአጸዱን የማዘመን ሥራዎችን የሚያካትት ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ግንባታው በሁለት ፈረቃ ተከፍሎ በከፍተኛ ጥንቃቄ እየተከናወነ 40 በመቶ ያህሉ መጠናቀቁ ተገልጿል።
ለዚህ ግዙፍ የዕድሳት ሥራ ከ134 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደሚያስፈልግ የተጠቆመ ሲሆን፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብጹዕ አቡነ ሳዊሮስ በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ምዕመናን በገዳሙ ስም በተከፈቱ የባንክ ሒሳቦች አማካኝነት በገንዘብ፣ በጸሎትና በጉልበት ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
