በመመሪያው መሠረት የነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች ለማንኛውም የነዳጅ ዓይነት አቅርቦት ለሚከተሉት አካላት ቅድሚያ እንዲሰጡ ታዟል ፦
– ለፀጥታ ተቋማት፣ ቁልፍ ለሆኑ የመንግስት ፕሮጀክቶች እና በተለይም በመጠናቀቅ ላይ ላሉ የልማት ስራዎች።
– ለኢንዱስትሪዎች፣ መሠረታዊ ሸቀጦችን ለሚያመርቱ አምራች ድርጅቶች እና ምርታቸውን ወደ ውጭ ለሚልኩ ተቋማት።
– ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለሚታይባቸው እና የሀገር አቋራጭ የትራንስፖርት ፍሰት ላለባቸው የኮሪደር አካባቢዎች።
የነዳጅ ቸርቻሮ ማደያዎች ለሕዝብ ትራንስፖርት ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ እንዲሰጡ የታዘዘ ሲሆን፣ ነዳጅ ቁጠባውን ለማጠናከርም አዲስ ክልከላ ተጥሏል።
በዚህም መሠረት ከፋብሪካው ከተገጠመላቸው የነዳጅ ማጠራቀሚያ (ሰልቫቲዮ) ውጭ፣ ተጨማሪ ሰልቫቲዮ አስገጥመው የሚመጡ አሽከርካሪዎችን ማደያዎች እንዳያስተናግዱ እና መሰል ድርጊቶችን ለፀጥታ አካላት እንዲጠቁሙ መመሪያ ተሰጥቷል።
በተጨማሪም ነዳጅ የጫኑ ቦቴዎች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ (Timing Arrival) መሠረት መድረሻ ቦታቸው መድረሳቸውን ኩባንያዎች በጥብቅ እንዲከታተሉ ታዟል።
በነዳጅ አጓጓዥ ተሽከርካሪዎች ብልሽት እና በሾፌሮች የልምድ ማነስ በሚፈጠሩ አደጋዎች በሚከሰት የነዳጅ ብክነት እንዳይፈጠር ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ ለነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎች ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።
በነዳጅ ቸርቻሪ ማደያዎች በኩልም በከተማ አስተዳደር በክልል /ንግድ ቢሮዎች፣ በዞን/ በከተማ/ እና በወረዳ ንግድ ቢሮ/ ጽህፈት ቤት በኩል በደብዳቤ ለሚስተናገዱ ቀጥታ ተጠቃሚዎች የሚሰጠው ነዳጅ በጥንቃቄ እና ለታለመለት ዓላማ ብቻ መዋል እንዳለበት መመሪያው አሳስቧል።
ባለሥልጣኑ በመጨረሻም ይህንን መመሪያ ተግባራዊ በማያደርጉ እና በነዳጅ ግብይት ሂደት ላይ ሕገ-ወጥ ተግባር በሚፈጽሙ ማንኛውም ተዋናዮች ላይ በአዋጅ እና በመመሪያው መሠረት ጠንካራ እርምጃ እንደሚወሰድ እና ተጠያቂ እንደሚሆኑ በጥብቅ አስጠንቅቋል።
