አሜሪካ በካሪቢያን ባህር ላይ ባደረሰችው አዲስ ጥቃት አራት ሰዎች መገደላቸውን ፔንታጎን አስታወቀ።
የዩናይትድ ስቴትስ ጦር በካሪቢያን ባህር ላይ ዕፅ በማዘዋወር ላይ ነበረች ባላት ጀልባ ላይ ሌላ ገዳይ ጥቃት መፈጸሙን እና በዚህም አራት ሰዎች መገደላቸውን ነው የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስቴር (ፔምታጎን) ያስታወቀው።
የአሜሪካ ደቡባዊ ዕዝ (US Southern Command) በኤክስ (x ) ማህበራዊ ሚዲያ ባሰራጨው መግለጫ ጥቃቱን የመሩት የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሰት መሆናቸውን ገልጿል። በዚህም አራት ናርኮ ሽብርተኞች መገደላቸውን የገለጸው ዕዙ ጀልባዋ በታወቀ የዕፅ ዝውውር መስመር ላይ ሕገወጥ ዕፆችን ስታጓጉዝ እንደነበር በመረጃ ማረጋገጡን አክሏል።
ይህ አዲስ ጥቃት የተፈጸመው የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር በባህር ላይ እየወሰዳቸው ባሉት ወታደራዊ እርምጃዎች ሕጋዊነት ዙሪያ ጥያቄዎች በርትተው እየተነሱበት ባለበት ወቅት ነው።
በተለይም ባሳለፍነው መስከረም 2 በተፈጸመ ጥቃት ዒላማ የተደረገው ጀልባ ሁለት ጊዜ መመታቱ ከተገለጸ በኋላ አስተዳደሩ በሕጋዊነቱ ዙሪያ ለተነሱ ከባድ ጥያቄዎች መልስ እንዲሰጥ ግፊት እየደረሰበት ይገኛል።
ባለሙያዎች የተረፉ ሰዎችን ለመግደል ሁለተኛ ድብደባ መፈጸም ዓለም አቀፍ የጦርነት ሕግን የሚጥስ እና የጦር ወንጀል ሊያስከትል እንደሚችል እያስጠነቀቁ ይገኛል ።
አሜሪካ ከእነዚህ ቡድኖች ጋር በይፋ የታወጀ ጦርነት ላይ ባለመሆኗ ድርጊቶቹ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ሕግን የሚጥሱ እና ያለ ፍርድ የሞት ቅጣት እንደመስጠት የሚታይ ነው ሲሉ ባለሙያዎች በመግለፅ ላይ ናቸው ።
አሜሪካ በበኩሏ ጥቃቱን የፈጸመችው በሽብርተኛ ድርጅት ላይ እንደሆነ እና የተገደሉትም “ናርኮ-ሽብርተኞች” እንደሆኑ በተደጋጋሚ ገልጻለች።
ዘገባው አልጄዚራ ነው
