የትራምፕ አስተዳደር ከአሜሪካ ኃይሎች ጋር አብረው የሠሩ አፍጋኒስታናውያን ወደ አሜሪካ እንዲዛወሩ የረዳውን ቁልፍ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቢሮ እያፈረሱ ነው ሲል ዘ ዋሽንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
በአሜሪካ የአፍጋኒስታን ቆይታ ወቅት በአስተርጓሚነት፣ ሾፌርነት እና የሲቪል ሠራተኞች ሆነው ያገለገሉትን አብዛኞቹን ጨምሮ ከ250 ሺህ በላይ አፍጋኒስታናውያን በአሁኑ ጊዜ በእንጥልጥል ላይ ይገኛሉ፡፡
በኳታር፣ ፓኪስታን እና በተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች በሚገኙ ካምፖች ውስጥ እንዲቆዩ የተደረጉ አንዳንዶች ደግሞ ታሊባን ወደሚመራት አፍጋኒስታን በግዴታ የመመለስ አደጋ አንዣቦባቸዋል፡፡
የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች፤ አሜሪካ የስደተኞች ማመልከቻ ሂደትን እያዘገየች እና የሎጂስቲክስ ድጋፍ እያቋረጠች መሆኑን ተከትሎ ከአፍጋኒስታን እንዲወጡ የተደረጉ ሰዎችን ወደነበሩበት መመለስ መጀመሯን ለዘ ዋሽንግተን ፖስት የደረሰው መረጃ ያሳያል፡፡
