በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር በዋሉት የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) አመራሮች እና አባላት ፦ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አቶ ይስሐቅ ወልዳይ፣ አቶ አበበ አካሉ እና ጠበቃ አበራ ንጉሥ ላይ ሐሙስ ነሐሴ 28 2018 ዓ.ም በዋለው ችሎት መርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው ለችሎቱ ጥያቄ አቅርቦ ነበር።
ተጠርጣሪዎቹ በአርባ ምንጭና በአዲስ አበባ ሕገወጥ አደረጃጀት በመፍጠር ሕገመንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ ተንቀሳቅሰዋል ያለው ፖሊስ፤ ከአርባ ምንጭ የሕክምና ማስረጃ ለማምጣት፣ የፎረንሲክና የባንክ እንቅስቃሴ ውጤቶችን ለማጠናቀቅ ተጨማሪ 14 ቀን ያስፈልገኛል ሲል ዋስትናቸውን ተቃውሟል።
የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው ደንበኞቻቸው ከአንድ ወር በላይ በእስር መቆየታቸውን፣ የሚጠበቁት ማስረጃዎች ከመንግሥት ተቋማት የሚመጡ በመሆናቸው በዋስ ቢወጡ የሚያጠፉት ማስረጃ እንደሌለ፣ እንዲሁም ከአገር እንዳይወጡ የእግድ ትእዛዝ ማውጣት እንደሚቻል በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ተከራክረዋል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት የግራ ቀኙን ክርክር ካዳመጠ በኋላ፣ ለነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር።
በዚሁ መሠረት ፍርድ ቤቱ አርብ ነሐሴ 29 2018 ዓ.ም በዋለው ችሎት ተጠርጣሪዎቹ እያንዳንዳቸው በ50 ሺህ ብር ዋስ እንዲፈቱ መወሰኑን ከጠበቃቸው ከአቶ ሰለሞን ገዛኸኝ ሰምተናል።
