የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (CPJ) የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት የአዲስ ስታንዳርድ (Addis Standard) አዘጋጅ ሚሊዮን በየነን ፈልጎ ለማግኘት እና ለማስፈታት አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ እንዲያደርጉ ጥሪ አቀረበ።
ሚሊዮን ረቡዕ ጠዋት በመዲናዋ አዲስ አበባ ከሚገኘው ቢሮው ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ተወስዷል።
ሲቪል ልብስ የለበሱ፣ አንዳንዶቹ ቆብና የፊት መሸፈኛ (mask) ያደረጉ ሰዎች ሚሊዮንን አፍነው መውሰዳቸውን አሳታሚ ድርጅቱ ገልጿል።
የሲፒጄ (CPJ) የአፍሪካ ፕሮግራም አስተባባሪ ሙቶኪ ሙሞ ባስተላለፉት መልእክት፡-
“የሚሊዮን በየነ ከአዲስ ስታንዳርድ ቢሮ ታፍኖ መሰወር፣ ባለሥልጣናት በየካቲት ወር የአሳታሚውን የምዝገባ ፈቃድ ከሰረዙ በኋላ በዲጂታል ሚዲያው ላይ እየደረሰ ላለው ችግር አሳሳቢ አዲስ ምዕራፍ ነው።
የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ሚሊዮን በየነን ማን አፍኖ እንደወሰደው በአስቸኳይ ማረጋገጥ፣ እንዲለቀቅ ማድረግ እና ጥፋተኞችንም ተጠያቂ ማድረግ አለባቸው። ” ብለዋል።
የፌዴራል ፖሊስ ቃል አቀባይ ጄይላን አብዲ ስለ ሚሊዮን ደብዛ መጥፋት ከሲፒጄ ተጠይቀው፣ ሚሊዮን በፌዴራል ፖሊስ ቁጥጥር ሥር አለመሆኑን ቤተሰቦቹ ማረጋገጣቸውን በዋትስአፕ (WhatsApp) በኩል ገልጸዋል።
ጉዳዩ እየተመረመረ መሆኑን በተመለከተ ለቀረበላቸው ጥያቄ ግን ቀጣይ ጥያቄዎች ለአዲስ አበባ ፖሊስ እንዲቀርቡ ምላሽ ሰጥተዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ቃል አቀባይ ማርቆስ ታደሰ ለሲፒጄ በላኩት የጽሑፍ መልእክት የከተማዋን ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ቶማስ እሸቴን እንዲያነጋግሩ የመሩ ሲሆን፣ አቶ ቶማስ ግን በስልክ ባደረጉት ምልልስ ምንም ዓይነት መረጃ እንደሌላቸው ተናግረዋል።
