የአያልነህ ሙላቱ የስነ-ጥበብ የአደራ የበጎ አድራጎት ድርጅት “ሀገር በቀል እውቀት ለሀገር ያለው ፋይዳ ምንድን ነው?” በሚል መሪ ቃል ያዘጋጀው የጥናት መድረክ የፊታችን ማክሰኞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ።
በጉዳዩ ላይ መግለጫ የሰጡት አንጋፋው ጸሐፌ ተውኔትና ባለቅኔ ጋሽ አያልነህ ሙላቱ፣ ወቅታዊው ሥልጣኔ በባህል ላይ ያልተመሰረተ በመሆኑ የራሳችንን ጥለን የሌላውን አንጠልጥለን ለመጓዝ መገደዳችንን ገልጸዋል።
የቀደምት አያቶቻችን ጥበብ የት እንደሄደ መጠየቅ ይኖርብናል ያሉት ጋሽ አያልነህ፣ ባለማወቅ የጣልናቸውን እውቀቶች አንስተን ለሀገር ያላቸውን ጠቃሚነት ማየት እንደሚገባ አሳስበዋል።
የፊታችን ማክሰኞ ሚያዝያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም በሚካሄደው በዚህ ታላቅ መድረክ ላይ በዩኒቨርሲቲ ምሁራንና በዘርፉ ሊቃውንት የተዘጋጁ 13 ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ።
በዕለቱም ፊደል፣ ጽሑፍና ንባብ በኢትዮጵያ፣ የሀገር ባህል ሕክምና በኢትዮጵያ እንዲሁም ባህላዊ የግጭት አፈታትና የዕርቅ ሥርዓት በኢትዮጵያ የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች በዋናነት ተዳስሰው ለውይይት እንደሚቀርቡ ታውቋል።
የድርጅቱ የቦርድ ዋና ጽሐፊ ግርማዊ ፍቃዱ እንደጠቆሙት፣ ጥናታዊ ጽሑፎቹ በዘርፉ ሰፊ እውቀት ባላቸው ምሁራን የቀረቡ መሆናቸው ለውይይቱ ከፍተኛ ግብዓት ይኖረዋል።
ይህ የጥናት መድረክ ከረፋዱ 03፡00 ጀምሮ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በማንዴላ አዳራሽ የሚከናወን ሲሆን፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ እንግዶችና ታዳሚዎች በሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደሚገኙ ይጠበቃል።
