የኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.ኤ.አ ከሚቀጥለው የካቲት ወር ጀምሮ ከአዲስ አበባ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ የወደብ ከተማ ጂዛን ቀጥታ በረራ ሊጀምር መሆኑን ይፋ አድርጓል።
አየር መንገዱ የቱሪዝም መዳረሻ ወደ ሆነችው ጂዛን ከተማ የሚጀመረው የመንገደኞች በረራ ለቱሪስትች እና ለንግድ ሥራ አንቀሳቃሾች ጥሩ ዕድል የሚፈጥር ነው ተብሏል።
አየር መንገዱ ከአዲስ አበባ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ የሚጀምረው 5ኛው የበረራ መዳረሻ በአፍሪካ እና በመካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት መካከል ያለውን የቱሪዝም የንግድ እና የሕዝብ ለህዝብ ግንኙነት ለማጠናከር ያግዛል ብሏል።
አየር መንገዱ በአሁኑ ሰዓት በሳዑዲ ዓረቢያ ወደ ጅዳ፣ ሪያድ፣ ደማምና መዲና አራት መዳረሻዎች በሳምንት ውስጥ 40 የበረራ አገልግሎቶችን እየሰጠ ይገኛል።
ተቋሙ ከተለያዩ ሀገራት አየር መንገዶች ጋር ስምምነት በማድረግም ለተለያዩ ሀገራት በሚሰጠው አስተማማኝ የአየር ትራንስፖርት መልካም ስም መገንባት ችሏል።
በአፍሪካ ከ60 በላይ በዓለም ከ145 በላይ መዳረሻዎች ያሉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ አፍሪካን ከዓለም በአየር ትራንስፖርት በማገናኘት የአንበሳውን ድርሻ ይዟል።
