የኢትዮጵያ ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በካቻ ዲጂታል ፋይናንሻል ሰርቪስ አክሲዮን ማኅበር የባንክ ሒሳቦች ላይ ተጥሎ የነበረው እግድ ሙሉ በሙሉ እንዲነሳ ትዕዛዝ አስተላለፈ። ይህ ውሳኔ ኩባንያው ሁሉንም የሥራ ማስኬጃ ሒሳቦቹን በመጠቀም መደበኛ የንግድ እንቅስቃሴዎቹን እንዲቀጥል ያስችለዋል።
እንደ ችሎቱ ውሳኔ፤ ከውርርድ ተግባር ጋር በተያያዘ በምርመራ ላይ ያለው ሦስት ሚሊዮን ብር ገደማ ብቻ ተለይቶ ታግዶ እንዲቆይ ተወስኗል።
ይህ የተጠቀሰው ገንዘብ እየተካሄደ ያለው ምርመራ ውጤት እስኪታወቅ ድረስ ታግዶ የሚቆይ ሲሆን፣ የቀሩት የኩባንያው ሒሳቦች ግን ከማንኛውም እግድ ነፃ ሆነዋል።
ፍርድ ቤቱ በሰጠው ውሳኔ ላይ ምርመራው በሚቀጥልበት ወቅት ኩባንያው የንግድ ሥራውን ለማስቀጠልና የደንበኞቹን ፍላጎት ለማሟላት ያልተገደበ የሒሳብ እንቅስቃሴ አስፈላጊ መሆኑን አፅንዖት ሰጥቷል።
በዚህም መሠረት በሁሉም የፋይናንስ ተቋማት የሚገኙ የካቻ ሒሳቦች አሁን ሙሉ በሙሉ ክፍት ተደርገዋል። ባንኮች እና የሚመለከታቸው አካላት የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በአፋጣኝ እንዲያስፈጽሙ የታዘዘ ሲሆን፤ ይህም ካቻ ያለምንም መስተጓጎል የገንዘብ ልውውጦችን እንዲያከናውን፣ የደንበኞችን ገንዘብ እንዲያስተዳድር እና አስፈላጊ ክፍያዎችን እንዲፈጽም ዕድል ይሰጠዋል።
ካቻ ዲጂታል ፋይናንሻል ሰርቪስ በአገሪቱ የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት ላይ ከፍተኛ ተሳትፎ እያደረገ የሚገኝ ተቋም መሆኑ ይታወቃል።
