የዘንድሮው የዒድ አል-አድሀ (አረፋ) በዓል የዒድ ሰላት ሥነ ሥርዓት በሰላም እንዲጠናቀቅ ምዕመናኑ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ጥሪ አቅርቧል።
የጠቅላይ ምክር ቤቱ የዑለማ ጸሐፊ ሼህ መሐመድ ዘይን በበዓሉ ዕለት አረጋውያን እና ሕፃናት ስለሚኖሩ ግፊያና መሯሯጥን መቀነስ እንዲሁም የመስገጃ ቦታዎችን በጥንቃቄና በንጽህና መያዝ እንደሚገባ አሳስበዋል።
መሄጃና መመለሻ መንገዶች የተለያዩ እንደሚሆኑም አንስተው የመንገድ መዘጋጋት እንዳይፈጠር ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
ሼህ መሐመድ ለዒድ አል አድሀ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት በማስተላለፍ፥ በዓሉን እንደተለመደው ያለው ለሌለው በማካፈል ማክበር እንደሚገባ ጠይቀዋል።
በተመሳሳይም በአዲስ አበባ ስታዲየም እና በተለያዩ የክፍለ ከተማ መስገጃ ስፍራዎች ሥነ-ሥርዓቱ በሰላምና በደመቀ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አስታውቋል።
የምክር ቤቱ የአስተዳደር ጉዳዮች እና የተቋማዊ ልህቀት ምክትል ፕሬዝዳንት ኡስታዝ ሺሃቡዲን ሼህ ኑራን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፥ በዓሉ የእምነቱ ተከታዮች ለአላህ ያላቸውን ፍጹም ታዛዥነትና ታላቅ መስዋዕትነት የሚገልጹበት በመሆኑ ምዕመናኑ ማኅበራዊ አንድነትን በተግባር ሊያሳዩ እንደሚገባ ገልጸዋል።
የዘንድሮው የዒድ ሰላት ጠዋት 2፡00 ሰዓት ስለሚጀመር መላው የከተማዋ ሙስሊም ከሱብሂ ሰላት ጀምሮ በመንቀሳቀስ በስፍራው እንዲገኝ ጥሪ ቀርቧል።
