የአዲሱ የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ካርዲናል ሮበርት ፕሪቮስት በዓለ ሲመት በቅዱስ ፔጥሮስ አደባባይ ተካሂዷል።
በ100 ሺህ የሚቆጠሩ የእምነቱ ተከታዮች በተገኙበት በዓለ ሲመት ላይ የቅዳሴ እና የፀሎት ሥነ-ሥርዓት ተደርጓል።
በመርሐ-ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት ሊዮ 14ኛ፥ የደካሞች ብዝበዛ እንዲቆም፤ እንድንዋደድ እና አንድ እንድንሆን ያስፈልጋል፤ ፈጣሪም የሚሻው እርሱን ነው ሲሉ ተናግረዋል።
በካቶሊክ እምነት ውስጥ ‘የኃይማኖት ፕሮፖጋንዳ’ ቦታ እንደሌለው ጠቅሰው፤ መከፋፈል እና ፖለቲካዊ ጫና ከእምነት ውስጥ ሊወገዱ የሚገባቸው ጉዳዮች ናቸው ብለዋል።
አያይዘውም፥ የምድርን የተፈጥሮ ሃብት ብሎም ደካሞችን የሚበዘብዝ የኢኮኖሚ ሥርዓት መገታት እንዳለበት ገልፀዋል።
በንግግራቸው መጨረሻ ለዩክሬን ዘላቂ ሰላም ተመኝተው፤ በጋዛ ወዳጅ ቤተሰቦቻቸውን ያጡ ወገኖችን በፀሎት አስበዋል።
በመርሐ-ግብሩ ላይ የአሜሪካ ምክትል ፕሬዚዳንት ጄዲ ቫንስ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ፣ የፔሩ ፕሬዚዳንት ዲና ቦሉዋርቴ እና የዩክሬን ፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪን ጨምሮ ከ150 በላይ የሀገራት ተወካዮች ተገኝተዋል።
