በዘርፉ ያለውን የኃይል ስብጥር ለማሳደግና የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን ለማስፋት የግል አልሚዎች እንዲሳተፉ የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ መገባቱን የኢትዮጲያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታውቋል፡፡
በየዓመቱ የሀገሪቱ የኃይል ፍላጎት በአስር በመቶ እያደገ መሆኑን ያነሱት የተቋሙ የትራንስሚሽን እና ቢዝነስ ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አንዷለም ሲዓን፤ ከታሪፍ ማሻሽያው ጎን ለጎን የግል አልሚዎች እንዲሳተፉ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ይሁን እንጂ በሀገሪቱ ያለው ዝቅተኛ የኤሌክትሪክ የታሪፍ ምጣኔ የግል አልሚዎችን የሚያበረታታ ባለመሆኑ እስከ አሁን የሚፈለገው ውጤት አለመገኘቱ ተገልጿል፡፡
ከአሁን ቀደም ተቋሙ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወስዶት የነበረውና በተቋሙ የፋይናንስ ቁመና ላይ ከፍተኛ ጫና ፈጥሮ የቆየውን ብድር መንግሥት ወደ ራሱ መውሰዱም ተነስቷል፡፡
ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ተቋሙ የመክፈል አቅሙንና ገቢውን ያገናዘበ ብድር ከባንኩ በመውሰድ ፕሮጀክቶችን በራሱ አቅም ለማስፈፀም እየሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
የኔታ ቲዮብ
