አሸናፊ ግርማ የእግር ኳስ አካዳሚ አዋርድ በቀድሞ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ኮከብ አሸናፊ ግርማ ሀሳብ አምንጪነት ፣ የእግርኳስ ቤተሰቡን ለማበረታታት እና እርስ በርስ ያላቸውን መከባበር ለማሳደግ ያለመ “አሸናፊ ግርማ የእግር ኳስ አካዳሚ አዋርድ” የሽልማት መርሃ ግብር በዛሬው ዕለት ተካሄደ።
ይህ የሽልማት መርሃ ግብር ሀሳቡ ከተፀነሰ ሁለት አመታትን ያስቆጠረ ሲሆን፣ ዋና አላማውም የነገዎቹን ኮከቦች ከማፍራት ጎን ለጎን በኢትዮጵያ ስፓርት የራሳቸውን አሻራ ላስቀመጡ እና አሁንም ከፍተኛ እበርክቶ ላላቸው የዘርፉ ተዋናዬች እውቅና መስጠት እና መሸለም ነው ተብሏል።
አዘጋጁ እንዳሉት በሀገራችን የስፖርተኛው አዋርድ በበቂ ሁኔታ ስለሌለ፣ ስፖርተኞች እርስ በርስ ሊደጋገፉ እና እውቅና ሊሰጣጡ ይገባል በሚል እምነት ”በድንግል ማርያም እርዳታ እና በእግዚአብሔር ፈቃድ” ይህን መድረክ መጀመራቸውን ገልጸዋል።
ዘንድሮ በተካሄደው የመጀመሪያው መርሃ ግብር ላይ የተለያዩ ስፖርተኞች በነበራቸው አስተዋፅኦ በተለይም በክለብ እና በሀገር ደረጃ ጥሩ አቋም ያሳዩ ተጫዋቾች፣ ግብ ጠባቂዎች ፣ አሰልጣኞች እና ጋዜጠኛ ተመርጠው እውቅና ተሰጥቷቸዋል።
በዚህ መሠረት አንዋር ሲራጅ ፣ካሊድ መሀመድ፣ አዳነ ግርማ ፣ገብረመድህን ኃይሌ ፣አብርሃም መብራቱ ፣ጋዜጠኛ ጥሩነህ ካሳን ጨምሮ 12 ግለሰቦች ሽልማታቸውን ተረክበዋል።
በቀጣዩ አመት መርሃ ግብር ላይ ዘንድሮ ያልተካተቱትን ኮከብ የእግርኳስ ተጫዋቾችን የማካተት እቅድ መያዙ የታወቀ ሲሆን በቅርብ ዓመታት ውስጥ ሽልማቱን በማሳደግ የመኪና ባለቤት እስከማድረግ የሚያደርስ ትልቅ ራዕይ እንዳለ እና ለዚህም ከባንኮች ጋር በጋራ ለመስራት መታቀዱ ተጠቁሟል።
ምንም እንኳን በዚህ ዙር ሁሉም ተሸላሚዎች የገንዘብ ሽልማት ባያገኙም፣ አንዳንድ ልዩ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ተሸላሚዎች የገንዘብ ማበረታቻ ተሰጥቷቸዋል።
የኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሸብር ይህንን ጅምር በማድነቅ ለጥቂት ተሸላሚዎች የተለያየ መጠን ያላቸው የገንዘብ ስጦታዎች እንዲሁም ለሽልማት መርሃ ግብሩ የአንድ ሚሊዮን ብር ስጦታ ከኦሎምፒክ ኮሚቴው እንዲሁም በግላቸው እንደሚጡ ቃል ገብተዋል።
በመጨረሻም የኹነቱ አዘጋጅ አሸናፊ ግርማ ለዝግጅቱ መሳካት አስተዋፅኦ ያበረከቱ አካላትን አመስግነው ይህ ዝግጅት በየአመቱ እንደሚካሄድ እና ይሄም የስፖርቱን ቤተሰብ አንድነት የተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚያደርሰው ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል።
ከበደ መክብብ
