ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዩናይትድ ስቴትስ ለጋዛ ባወጣችው 20-ነጥብ ዕቅድ ላይ ሀማስ ተስማምቶ ስምምነት ላይ እንዲደርስ እስከ እሑድ ጊዜ ሰጥተዋል።
ሮይተርስ እንደዘገበው ከሆነ ትራምፕ ዓርብ ዕለት በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ ሀማስ እስከ እሑድ ምሽት 6፡00 ሰዓት (በዋሽንግተን ሰዓት) ድረስ ብቻ ጊዜ ምላሽ እንዲሰጥ ቀነ ገደብ አስቀምጠዋል።
ይህ የመጨረሻ ዕድል ስምምነት ላይ ካልተደረሰ፣ ማንም አይቶት የማያውቅ ሁሉን አቀፍ ሲኦል በሀማስ ላይ ይከፈታል” ብለዋል።
ትራምፕ በቅርቡ ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር በንያሚን ኔታንያሁ ጋር በዋይት ሀውስ ከተገናኙ በኋላ የ20-ነጥብ ዕቅዳቸውን ይፋ ያደረጉ ሲሆን፣ ዕቅዱም ለሀማስ አስቀድሞ ተላልፏል።
የዕቅዱ ይዘት
* የሀማስ ትጥቅ መፍታት
* እስረኞች በ72 ሰዓታት ውስጥ እንዲፈቱ
* የእስራኤል ወታደሮች ከጋዛ ቀስ በቀስ ሙሉ በሙሉ እንዲወጡ
* ከጦርነቱ በኋላ በትራምፕ መሪነት የጊዜያዊ አስተዳደር አካል እንዲቋቋም ጥሪ ያቀርባል።
የሀማስ ምላሽ
ሀማስ በእስራኤል በጋዛ ላይ እየተካሄደ ያለውን “የዘር ማጥፋት ጦርነት” ለማስቆም የአሜሪካውን ፕሬዝዳንት የ20-ነጥብ ዕቅድ ለማጥናት አሁንም ጊዜ እንደሚያስፈልገው ገልጿል።
የፍልስጤም የነጻነት ንቅናቄ ባለስልጣን ስማቸው እንዳይጠቀስ በመጠየቅ ዛሬ ለኤኤፍፒ እንደተናገሩት፣ “ሀማስ አሁንም የትራምፕን ዕቅድ ላየወ እያሰበ ሲሆን፣ አማላጆችን ምክክሩ በመካሄድ ላይ መሆኑን እና የተወሰነ ጊዜ እንደሚያስፈልገው ነግሯቸዋል” ብለዋል።
