በደቡባዊ ጅቡቲ ዲኺል ዞን በደረሰ ድንገተኛ ፍንዳታ አራት ሕፃናት መገደላቸውን የመንግሥት ባለሥልጣናት አስታወቁ።
የጅቡቲው ዓቃቤ ሕግ ሐሰን መሐመድ ሐሰን ክስተቱን “አሳዛኝ” ሲሉ የገለጹ ቢሆንም፣ የጅቡቲ የሰብአዊ መብቶች ሊግ ግን ጥቃቱ በሰው አልባ አውሮፕላን ወይም በድሮን የተፈጸመ መሆኑን አረጋግጧል።
ሕፃናቱ ከብት በመጠበቅ ላይ እያሉ በተሰነዘረው በዚህ ጥቃት፣ ዕድሜያቸው ከ6 እስከ 7 ዓመት የሆኑ ሁለት ሕፃናት ወዲያውኑ ሲሞቱ፣ ሌሎቹ ሁለቱ ደግሞ ተገቢውን ሕክምና ባለማግኘታቸው ሕይወታቸው አልፏል። በተጨማሪም ስድስት ንጹሐን ሰዎች ለከባድ እና ለቀላል አካል ጉዳት ተዳርገዋል።
የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ ጥቃቱ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ በዘላን ማኅበረሰቦች ላይ የተፈጸመ ስድስተኛው የድሮን ጥቃት መሆኑን ገልጾ፣ በፕሬዝዳንት ኢስማኢል ዑመር ጌሌ መንግሥት እና በአፋር ማኅበረሰብ መካከል ያለውን የቆየ የፖለቲካ ቅሬታ ይበልጥ እንዳባባሰው ተመልክቷል።
መንግሥት የፍንዳታውን መንስኤ ለማጣራት የባለሙያዎች ቡድን ወደ ስፍራው መላኩን ገልጿል።
