“ግራ ቀኝ” ተከታታይ ሲትኮም ድራማ ወደ ፊልም ተቀይሮ ሊሠራ እንደኾነ ተጠቆመ። በሀማ ቱማ በእንግሊዝኛ ተጽፎ በሕይወት ታደሰ “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ነገር” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ የተተረጎ መጽሐፍን መነሻ በማድረግ የተዘጋጀው “ግራ ቀኝ” ተከታታይ ሲትኮም ድራማ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሲቀረብ ቆይቷል። “ግራ ቀኝ” በተከታታይ ሲትኮም ድራማ መልክም በሁለት ምዕራፎች እና በ24 ክፍሎች የቀረበ ሲኾን አበበ ባልቻ፣ ግሩም ዘነበ፣ ሚካኤል ታምሬ ከተጋባዥ ተዋናዮች ጋር በጋራ ተውነውበታል። መስከረም 29 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ራስ መኮንን አዳራሽ ውስጥ የድራማው የምዕራፎች ማጠቃለያ መርሐግብርም ተካሄዷል። በምዕራፎቹ የማጠቃለያ ዝግጅት ላይም “ግራ ቀኝ” ተከታታይ ሲትኮም ድራማ ወደ ዘጠና ደቂቃ የሚፈጅ ፊልም ተቀይሮ ለተመልካቾች እንደሚቀርብ የድራማው አዘጋጅ ድርብድል አሰፋ ተናግሯል።
