አዲስ አበባ የኤሌክትሪክ አውቶብሶችን በማስተዋወቅ ወደ መጪው ዘመን የትራንስፖርት አገልግሎት እየተጓዘች ትገኛለች።
በቅርቡም በርካታ ቁጥር ያላቸው ዘመናዊ የኤሌክትሪክ አውቶብሶች በመዲናዋ አገልግሎት መጀመራቸው ይታወቃል።
በኤሌክትሪክ አውቶብሶቹ ውስጥ ተገልጋዮች በቀላሉ እና በዘመናዊ መልኩ በካርዳቸው ገንዘብ ከፍለው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያደርጋቸው ማሸን በመግቢያው በር ላይ ይገኛል።
ይህ በሌሎች ያደጉ አገራት የተለመደ ቀልጣፋ ሥርዓት ወደ አዲስ አበባ መምጣቱ አገልግሎቱን የበለጠ ምቹ አድርጎታል።
የአውቶብሶቹ አሽከርካሪዎች ካፒቴን በመባል የሚጠሩ ሲሆን ትኬት ቆራጮቹ ደግሞ ሆስተስ ተብለው ተሰይመዋል።
ኢቢሲ ዶትስትሪም እነዚህ አውቶብሶች ከሌሎቹ የተለየ ምን አዲስ ነገር ይዘዋል? አገልግሎታቸውስ በምን ይለያል? ሲል ጠይቋል።
የኤሌክትሪክ አውቶብስ አሽከርካሪዎች የሆኑት ካፒቴን ፍሬሕይወት ደምሴ እና ካፒቴን ዳዊት መስፍን አውቶብሶቹ ምቹ እና አስተማማኝ ብቻም ሳይሆን በፍጥነትም ከፍተኛ ብቃት አላቸው ይላሉ።
አውቶብሶቹ አዲስ ይዘትን ብቻ ሳይሆን አዲስ አገልግሎትን ይዘው ስለመከሰታቸውም ነው የሚናገሩት።
ካፒቴን ፍሬሕይወት ደምሴ፣ አውቶብሶቹ ከምቾታቸው ባሻገር ደኅንነታቸው የተጠበቀ በመሆኑ ሁሉም በራቸው በአግባቡ ካልተዘጋ ጉዞ አንደማይጀምሩ ነው የነገሩን።
ካፒቴን ዳዊት መስፍን ደግሞ፣ አውቶብሱ ምቹ እና ፈጣን በመሆኑ ተገልጋዮች በአገልግሎቱ ደስተኛ ናቸው ይላሉ።
የኤሌክትሪክ አውቶብስ የተገልጋዮችም ስለአገልግሎቱ አዎንታዊ አስተያየት ነው የሰጡት።
ተገልጋዮቹ አውቶብሶቹ ምቹ፣ ንፁህ እና ቀልጣፋ መሆናቸውን አድንቀዋል።
ብዙዎች በኤሌክትሪክ አውቶብሶች ውስጥ ያለው አገልግሎት በትህትና እና በቤተሰባዊ መንፈስ የተሞላ መሆኑንም ይናገራሉ።
በመዲናዋ ዘመናዊ እና ለአካባቢ ተስማሚ የሆነ የመጓጓዣ አማራጭ በማግኘታቸውም ደስተኞች መሆናቸውን ገልጸዋል።
ከአሽከርካሪዎችም ሆነ ከተገልጋዮች መረዳት አንደሚቻለው የኤሌትሪክ አውቶብሶች የአዲስ አበባ የወደፊት የትራንስፖርት ሥርዓት ቁልፍ አካል በመሆን የመላ ሀገሪቱን የወደፊት ጉዞ እያመላከቱ ነው።
