ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ስር የዋሉት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 6 ዳንኤል ጋራዥ አካባቢ ከሚገኘው ዲዛ (ቁርጥራጭ ብረት መሸጫ) ቤት ውስጥ ነው።
ተጠርጣሪዎች በረከት ብዙነህ፣ ሱፌ ገረመው፣ መንገሻ ኤቢሳ እና ስንታየሁ እሸቱ የተባሉ ሲሆን በዋና ወንጀል አድራጊነት የተጠረጠረው በረከት ብዙነህ፣ የተባለው ግለሠብ ጥር 13 ቀን 2017 ዓ/ም ግምታቸው 13 ሚሊዮን ብር የሚሆን ሁለት የዝሆን ጥርሶችን ከወላይታ ሶዶ ወደ አዲስ አበባ በማምጣት በክፍለ ከተማው ወረዳ 5 ውስጥ ከሚገኝ አንድ ግለሰብ ቤት በአደራ አስቀምጦ ገዢ እያፈላለገ እንደነበር የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገልጿል።
ግለሰቡም ከሁለት ደላሎች ጋር በመነጋገር አንዱን ኪሎ በ350ሺህ ብር ለመሸጥ በመስማማት ኮድ 2 C- 06326 አ/አ ዲ.ኤክ.ስ ተሽከርካሪ በመጠቀም በክ/ከተማው ወረዳ 6 ዳንኤል ጋራዥ አካባቢ ከሚገኘው ዲዛ ቤት በመውሰድ እያስመዘኑ እያለ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት እና የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ አባላት በደረሳቸው ጥቆማ ግንቦት 2 ቀን 2017 ዓ/ም ተጠርጣሪዎቹ እጅ ከፍንጅ መያዛቸውን የወንጀል ምርመራ መዝገቡ ያስረዳል።
ተገቢውን ምርመራ በማጣራትና መዝገቡን በማደራጀትም ለፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ መላኩንም ፖሊስ መምሪያው ገልጿል።
