“እንኳን ግብር ልንከፍል ልጆቻችንን መመገብ አቅቶናል”

Date:

                                             

በደቡብ ወሎና ሰሜን ወሎ ዞን ከ60ሺህ የሚልቁ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አሉ፡፡ አብዛኛዎቹ ከአምስት ዓመት በፊት  በኦሮሚያ ክልል በተፈጠረ የጸጥታ ስጋት ቀያቸውን ትተው የተሰደዱ ናቸው፡፡ ተፈናቃዮቹ፤  ያለባችሁን ግብር የማትከፍሉ ከሆነ መሬታችሁን ለሌሎች እናስተላልፋለን ተብለናል ሲሉ ለዶቸ ቬለ ተናግረዋል፡፡

“አሁን እንኳን ግብር ልንከፍል ልጆቻችንን  መመገብ አቅቶናል” ብለዋል ተፈናቃዮቹ፡፡

ከ5 ዓመታት በፊት በኦሮሚያ ክልል በተከሰተ የፀጥታ ችግር አካባቢያቸውን ለቀው የተሰደዱና በአማራ ክልል የሚኖሩት እነዚህ  ተፈናቃዮች፤ ተቃጥሎ ጥለነው ለመጣነው ቤትና ለዓመታት ሳይታረስ ለቆየ የእርሻ መሬት ግብር ክፍሉ እየተባልን ነው ሲሉ ቅሬታቸውን ገልጸዋል፡፡

በጃራ  የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የሚኖር  አንድ ለደህንነቱ ሲል ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ  ተፈናቃይ፣ በምስራቅ ወለጋ ሆሮ ጉድሩ ጃርቴ ወረዳ የሚገኝ መሬቱን፣ ነገ ሰላም ከመጣ አርሰዋለሁ በሚል ከተሰጠው እርዳታ ላይ ቀንሶ  ግብር መክፈሉን ለዶቸ ቬለ ተናግሯል፡፡

‹‹መሬቱ ብቻ ነው ያለው፤ ቤቱ ሁሉ ተቃጥሏል፤ ሀብት ንብረቱ ወድሟል፤ መሬቱ እንኳን ለልጆቼ ይትረፍ  ብዬ  ከተሰጠኝ እርዳታ፣ ከእለት ጉርሻዬ ላይ ቀንሼ 4100 ብር ከፍያለሁ ›› ብሏል፤ ተፈናቃዩ፡፡

በምስራቅ ወለጋ ዞን ጃርቴ፣ኡሙሩና ኬረሙ ወረዳ ነዋሪ የነበሩት ተፈናቃዮች፤ ነገ መሬታችንን ላለማጣት ስንል አቅም ያለው ብር እየላከ፣ ግብር እየከፈለ ቢሆንም፣ አብዛኛው ተፈናቃይ ግን የመክፈል አቅም የለውም ብለዋል፡፡

አሁን ያለባችሁን ግብር የማትከፍሉ ከሆነ፣ መሬታችሁን  ለሌሎች እናስተላልፋለን የሚል ማስጠንቀቂያ እንደደረሳቸውም  ነው ተፈናቃዮቹ የሚናገሩት፡፡

አካባቢው ሰላም ቢሆንና ለእኛም የመኖር ዋስትና ቢሰጠን በዚህ መጠለያ ጣቢያ ውስጥ መቆየት አንፈልግም የሚሉት ተፈናቃዮቹ፤ አሁን  ባለንበት ሁኔታ ግን እንኳን ግብር ልንከፍል ቀርቶ ለልጆቻችን ምግብ ማብላት አቅቶናል ብለዋል፡፡

ለምንበላውና ለምንጠጣው የመንግሥትን  እጅ የምንጠብቅና  በመጠለያ ውስጥ የምንኖር ተፈናቃዮች ነን ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ግብር የምንከፍልበት አቅም እንደሌለን መንግሥት ሊረዳን  ይገባል ብለዋል፡፡

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

ግዮን መጽሔት ዛሬ ቅዳሜ ግንቦት 1 2018 ዓ.ም ገበያ ላይ ውሏል !!!

በኢትዮጵያ ነፃ ኘሬስ ከ25 ዓመት በላይአገልግለናል !!! -የአርበኞች አደራና የትውልዱ...

ከሌ/ጄነራል ታደሰ ወረደ የተላለፈ ጥሪ

በክልላችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያደገ የመጣው የተሳሳተ ስሌት የወለደው...

በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ላይ በከባድ መሳሪያዎች የታገዘ  የተኩስ ልውውጥ ተካሄደ

ለዓለም የንግድ ሰንሰለት እጅግ ስትራቴጂካዊ በሆነው የሆርሙዝ ባህረ ወሽመጥ...

የሲ.ኤን.ኤን መስራች ቴድ ተርነር ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ

የዓለማችን ግዙፍ የዜና አውታር ሲኤንኤን መስራች ቴድ ተርነር በ87...