የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለመቄዶንያ 30 ሚሊዮን ብር አበረከተ
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ እቤ ሳኖ 30ኛ ቀኑን በያዘው የመቄዶንያ የእርዳታ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ላይ በመገኘት የባንኩን ድጋፍ አበርክተዋል።
አቶ አቤ እንዳሉት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሠራተኞች እና ማኔጅመንት አባላት የተሰበሰበ 18 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ባንኩ 12 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ በድምሩ 30 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ተደርጓል።
አቶ አቤ መቄዶንያ እያከናወነ የሚገኘው የበጎ አድራጎት ስራ የሚደነቅ እና የሚበረታታ መሆኑን ገልጸው፣ ባንኩ እንደሁልጊዜው ሁሉ ከማእከሉ ጎን እንደሚቆም ተናግረዋል።
አቶ አቤ ሁሉም ዜጋ እንደየአቅሙ ለማዕከሉ ድጋፍ እንዲያደርግም ጥሪ አቅርበዋል።
የመቄዶንያ መስራች እና የበላይ ጠበቂ የክብር ዶክተር ቢኒያም በለጠ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የመቄዶንያ ቋሚ ደጋፊ መሆኑን ገልጸው፣ በየጊዜው ለማዕከሉ ለሚያደርገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአሁኑን ድጋፍ ሳይጨምር ከዚህ በፊት በተለያዩ ጊዜያት ለማዕከሉ 205 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ማድረጉ ይታወሳል።
