መንግሥት በፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን በከፍተኛ ጥበቃ፣ በዝዋይ፣ በድሬዳዋ፣ በሸዋ ሮቢት፣ በቀጠሮ እና በሴቶች ማረሚያ እና ማረፊያ ማዕከላት ውስጥ በእርምት ሂደት ላይ ለነበሩ እና የባህሪ መሻሻል ላሳዩ፤ 541 የሕግ ታራሚዎች በይቅርታ ወደ መጡበት ማህበረሰብ እንዲቀላቀሉ መደረጉ ተገልጿል፡፡
በፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሸን የታራሚዎች ፍትህ አስተዳደር ዳይሬክተር ረ/ኮሚሽነር ሲሳይ ሃይለ እየሱስ፤ ለሕግ ታራሚዎች ይቅርታ የሰጠው ይቅርታ ቦርድ ጉዳዩን ሲከታተል መቆየቱን ገልጸው፤ የባህሪ መሻሻል ላሳዩ 32 ሴት እና 509 ወንድ በድምሩ ለ 541 የሕግ ታራሚዎች ይቅርታ መሰጠቱን አረጋግጠዋል፡፡
ረ/ኮሚሽነር ሲሳይ አክለውም፤ ከማረሚያ ማዕከላት ውስጥ በይቅርታ የወጡ የሕግ ታራሚዎች በማረም ማነጽ ሂደት ውስጥ የባህሪ መሻሻል ያመጡ እና ጉዳያቸው በይቅርታ ቦርድ ውሳኔ ያገኘ መሆኑን መግለጻቸውን አሐዱ ከፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ያገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
በፍትህ ሚኒስቴር ዓቃቢ ሕግ ሱራፌል ደመላሽ በበኩላቸው፤ የሕግ ታሚዎች በፍርድ ቤት ውሳኔ መሰረት ወደ ማረሚያ ተቋማት የሚላኩት በማረምና በማነጽ የአመለካከት ለውጥ እንዲያመጡ ከማድረግ ባሻገር ተጨማሪ ወንጀል እንዳይፈጽሙ ለማድረግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
“ይቅርታ መንግሥት ለሕግ ታራሚዎች የሚሰጠው ችሮታ እንጅ መብት አይደለም” ያሉት ዐቃቤ ሕግ ሱራፌል፤ የይቅርታ እድሉን ያገኙ የሕግ ታራሚዎች አምራች እና ሕግ አክባሪ ዜጎች በመሆን የበደሉትን ማህበረሰብ ሊክሱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የይቅርታው ተጠቃሚ የሆኑት የሕግ ታራሚዎች በሰጣቸው የይቅርታ እድል ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፤ በእርምት ቆይታቸው ለቀጣይ ሕይወታቸው ስንቅ የሚሆን ግንዛቤ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
(አሐዱ ሬዲዮ)
