በኦሮሚያ ክልል 724 ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ መሆናቸው የተገለፀ ሲሆን ከዛ ዉስጥም 12ቱ ተጠናቀዉ ለምረቃ መዘጋጀታቸዉንና እስከ ሰኔ ተጠናቀዉ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆኑ የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ አስታዉቋል ።
38ቱ በተለያዩ የፀጥታ ችግር ግንባታቸዉ የተቋረጠ ሲሆን በአጠቃላይ በክልሉ የሚገኙ ሆስፒታሎች 120 መድረሳቸዉ ተገልጿል ። የመድኃኒት ፣የሰዉ ሀይል እና የህክምና ቁሳቁስ እጥረት ህዝቡ አሁን ላይ እያነሳ ያለዉ ጥያቄ በመሆኑ ይህን ለመቅረፍ 567 የህዝብ ፋርማሲዎች በከተማ ፣በወረዳ እና በሆስፒታል ደረጃ መስፋፋታቸውን የኦሮሚያ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶክተር ቦቆና ጉታ ተናግረዋል ።
ያጋጠመዉን የመድኃኒት አጥረት ሙሉ ለሙሉ ለመቅረፍ እንደ ክልል ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር ሰፊ ጊዜ በመዉሰድ መስራት እንደሚገባ የገለፁት ኃላፊዉ 80 በመቶ የሚሆነዉ መድኃኒት ከዉጪ የሚገባ በመሆኑ በሀገር ምርት መተካትና ለዚህ የሚዉለዉን በጀት መጨመር ትልቁ ለወደፊት የሚሰራ በዕቅድ የተያዘ ነዉ ብለዋል ።
ጤና ኬላዎችንና ጤና ጣቢያዎችን በማስፋፋት አዳዲስ አሰራሮችን በመዘርጋት በፊት ያልነበሩ 10 ሆስፒታሎች ዉስጥ የሲቲ ስካን አገልግሎት መጀመሩን ዶክተር ቦቆና ከጣቢያችን ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል።
@ብስራት ራዲዮ
