በ2017 በጀት ዓመት በመግቢያና መውጫ ኬላዎች ላይ በተደረገ ፍተሻና ቁጥጥር ወደ ሀገር ውስጥ ሊገቡ የነበሩና ሕገ-ወጥ ሆነው የተገኙ፤ ከ48 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ መድኃኒቶችና የመድኃኒት ጥሬ እቃዎች መወገዳቸውን የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን ለአሐዱ አስታውቋል።
በየትኛውም መግቢያና መውጫ ያሉ ባለሙያዎች ምርት ወደ ሀገር ከመግባቱ በፊት የተመዘገበና የቅድመ ማስገቢያ ፍቃድ ስለመኖሩ የፍተሻ ሥራ እንደሚሰሩ፤ በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የደቡብ ምስራቅ ቅርንጫፍ አዲስ አበባ የቃሊቲ መግቢያና መውጫ መሪ ሥራ አስፈፃሚ ወ/ሮ አለምነሽ አበራ ተናግረዋል።
በሕጋዊ መንገድ ከሚገቡት ባሻገር ደህንነታቸውና ፈዋሽነታቸው ያልተረጋገጡ እና በሕጋዊነት ከተመዘገቡት ጋር ተመሳስለው ሊገቡ የሚችሉ ሕገ-ወጥ መድኃኒቶች መኖራቸውንም አንስተዋል።
በዚህም መሠረት መድኃኒቶች እና የመድኃኒት ጥሬ እቃዎች መስፈርቱን ባለማሟላታቸው ምክንያት ወደ መጡበት ሀገር እንዲመለሱ አልያም እንዲወገዱ መደረጉን ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ በሚገኙ አምስቱም የመድኃኒት መግቢያና መውጫ ኬላዎች ላይ በሚደረግ ቁጥጥር መድኃኒቶችን ለናሙና በመውሰድ የሚመረመርበት አሰራር ስለመኖሩም መሪ ሥራ አስፈፃሚዋ አንስተዋል።
በዚህ ሂደትም ሕጋዊ ሆነው ተመዝግበው ነገር ግን መድኃኒቱ ከተቀመጠለት ደረጃ አንሶና በልጦ ከተገኘ ሕገ-ወጥ እንደሚሆን ተናግረዋል።
የሕገ-ወጥ መድኃኒቶችን ወደ ሀገር ውስጥ መግባት ከማስቀረትና ከመቆጣጠር አንፃር፤ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የፍተሻ እና የምርመራ ሥራዎች ተጠናክረው እየተሰሩ ስለመሆኑ ተናግረዋል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
