ለረጅም ጊዜ ሲጠበቅ የነበረው የኢትዮጵያ ሰነደ መዋዕለ ንዋዮች ( ስቶክ ገበያ) በሚቀጥለው ሳምንት ሥራ ሊጀምር መሆኑ ተሰምቷል። ይህ እርምጃ ለአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ ትልቅ ምዕራፍ እንደሆነ ታውቋል።
ገበያዉ በኖቬምበር 2023 በተደረገ የካፒታል ማሰባሰቢያ ዘመቻ 1.5 ቢሊዮን ብር በማሰባሰብ ከታሰበው ግብ በ631% በልጧል። ይህ ገንዘብ ከ48 የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተቋማት የተገኘ መሆኑ ይታወቃል።
በሕዝብና በግል ሽርክና የሚሰራው አዲሱ የበይነመረብ ንግድ ልዉዉጥ መድረክን መንግሥት 25%፣ የግል ዘርፍ ደግሞ 75% ድርሻ አላቸዉ። አሁን ላይ ገዳ ባንክ አ.ማ. እና ወጋገን ካፒታል ኢንቨስትመንት ባንክ አ.ማ. በገበያው ላይ ከተመዘገቡት ኩባንያዎች መካከል ይጠቀሳሉ።
የሰነደ መዋዕለ ንዋይ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ውስጥ እስከ 50 ኩባንያዎችን፣ በአሥር ዓመታት ውስጥ ደግሞ ከ90 በላይ ንግዶችን ለማካተት አቅዷል። ይህ ልውውጥ የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ለማዘመን፣ ግልጽነትን ለማሳደግ እና ለንግዶች ካፒታል ማሰባሰቢያ አዳዲስ አማራጮችን ለመስጠት ያለመ ሲሆን፣ የኢኮኖሚ ዕድገትን እንደሚያነቃቃም ይጠበቃል።
CapitalNews
