የስታርትአፕ አዋጅ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንድትሆንና ያላትን ዕምቅ አቅም በመጠቀም ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማስመዝገብ እንደሚያሰችል የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 2ኛ አስቸኳይ ስብሰባው፤ የኢትዮጵያ የስታርትአፕ አዋጅ አፅድቋል።
የሰው ሀብት፣ ሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ነገሪ ሌንጮ እንደተናገሩት፤ አዋጁ ምቹ የስታርታአፕ ምህዳርን በመገንባትና የተቀናጀ ድጋፍ መስጠት በሚያስችል መልኩ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል።
ረቂቅ አዋጁ የፈጠራ ባለሙያዎችን በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያበረታታ ተገልጿል። ትውልድ ራሱ ፈጥሮ፣ ራሱ አምርቶ ራሱ አቅራቢ እንዲሆን የሚያስችል ስለመሆኑ ተገልጿል።
አዋጁ በዓለም አቀፍ ደረጃ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ የተደገፉ ትላልቅ ኢንዱስትሪዎችንና ኩባንያዎችን በማፍራት ለኢኮኖሚ ዕድገትና ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ገልፀዋል።
የፋይናንስ አቅርቦት ተግዳሮትና ስጋትን በዘላቂነት ለመቅረፍ የግራንት ፕሮግራም፣ የብድር ዋስትና ማዕቀፍና መዋቅር ማደራጀት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።
በክብረአብ በላቸው
