በአማራ ክልል ከነሐሴ አጋማሽ ጀምሮ ሲከበሩ የቆዩት የቡሔ፣ የሻደይ፣ አሸንድየ፣ ሶለል እና እንግጫ ነቀላ በዓላት የማጠቃለያ መርሐ ግብር እየተካሄደ ነው።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልማህዲ በመርሐ ግብሩ ላይ እንዳሉት፥ የብሔር ብሔረሰቦች መገለጫ የሆኑ ባህሎች ሳይበረዙ ለትውልድ እንዲተላለፉና ኢትዮጵያዊ አብሮነትና አንድነትን የሚያስቀጥሉ እንዲሆኑ በትኩረት ይሰራል።
የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በዓላቱ በየአካባቢው ብቻ ተወስነው መቆየታቸውን አስታውሰው፥ የሀገር አቀፍና የዓለም አቀፍ እውቅና ባለቤት ለማድረግ በዚህ መንገድ መከበሩ ፋይዳው ትልቅ ነው ብለዋል።
የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ መልካሙ ጸጋዬ እንዳሉት፥ በዓላቱ ትውፊታቸውን ጠብቀው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ባለው መንገድ እንዲያድጉና ዓለም አቀፍ በዓላት ሁነው እንዲከበሩ እየተሰራ ይገኛል፡፡
ሕዝብ በአንድነትና በኅብረት የሚያከብራቸው በመሆኑ ለሰላም ያላቸው ፋይዳ ከፍ ያለ እንደሆነ ጠቅሰው፥ ማኅበረሰቡ በዓላቱን በመጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።
