የህክምና ኦክስጅን አቅርቦትና ተደራሽነትን በማሻሻል ሞትን መቀነስ የሚገባ መሆኑን የጤና ሚንስቴር ገለጸ። በሀገሪቱ ያሉ የኦክስጅን ማምረቻዎችን ከሦስት ወደ 58 ማሳደግ መቻሉንም የሚንስቴሩ ባለስልጣናት ገልጸዋል።
“የኦክስጅን ተደራሽነትን በማሻሻል ልንከላከል የምንችለውን ሞት እንቀንሳለን” በሚል መሪ ሃሳብ የዓለም የኦክስጅን ቀን ከሰሞኑ በኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ በተከበረበት ወቅት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ፍሬህይወት አበበ እንደገለጹት፤ የህክምና ኦክስጅን አቅርቦትን ጥራት እና ተደራሽነት በማሻሻል መከላከል ሞትን መቀነስ ይገባል።
የህክምና ኦክስጅንን በተገቢው መንገድ መጠቀም እና ቀጣይነት ያለው የኦክስጅን ሥርአትን ለመገንባት ከባለድርሻ አካላት ብዙ የሚጠበቅ መሆኑንም ሚንስትር ዲኤታዋ ገልጸዋል።
የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ በበኩላቸው “የህክምና ኦክስጅን አቅርቦት መሻሻሉ የእናቶችና ህጻናትን ሞትና ስቃይ በመቀነስ ሂደት ከፍተኛ ሚና አለው” ብለዋል።
የህክምና ኦክስጅን በቀዶ ህክምና፣ በጨቅላ ሕፃናት እና በአዋቂዎች ፅኑ ህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑን የጠቆሙት ዶ/ር ደረጀ፤ ይህንን ታሳቢ ያደረገ የኦክስጅን ማምረቻዎች ከነበረበተ 3 ወደ 58 ማሳደግ መቻሉንም ተናግረዋል።
(#አዲስ_ማለዳ)
