የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ዛሬ የአርጀንቲና አምባሳደርን ተቀብሎ በተወያየበት ወቅት አርጀንቲና በዘመናዊ የግብርና ስርዓት ያላትን ሰፊ ልምድ ለኢትዮጵያ እንድታካፍል ጥሪ ያቀረቡት በምክር ቤቱ የደቡብ አሜሪካና የካሪቢያን ፓርላማ ወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢ አብዱልቃድር ገልገሎ(ዶ/ር) ናቸው።
ቋሚ ኮሚቴው በኢትዮጵያና አርጀንቲና የረጅም ጊዜ ዲፕሎማሲያዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር እንዲሁም፣ በንግድ፣ በቴክኖሎጂ፣ በአቪዬሽን፣ በቱሪዝም እና በግብርና ዘርፎች ያላቸውን ሰፊ ትብብርና አቅም እንዲሁም የሁለቱ አገራት ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ከአርጀንቲና አምባሳደር ጁዋን ኢግናሲዮ ሮካታግሊታ ጋር ሰፊ ውይይት አድርጓል።
በውይይቱ ወቅት ኢትዮጵያ እና አርጀንቲና ረጅም ዓመታትን ያሰቆጠረ ታሪካዊና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው መሆኑን በምክር ቤቱ የደቡብ አሜሪካና የካሪቢያን ፓርላማ ወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢ አብዱልቃድር ገልገሎ(ዶ/ር) ገልጸዋል።
አርጀንቲና በዘመናዊ የግብርና ስርዓት ሰፊ ልምድ እንዳላት ያመላከቱት አብዱልቃድር (ዶ/ር)፤ ይሄንን ልምድ በተለይም በመካከለኛ ደረጃ ለሚገኙ የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች በማካፈል አርጀንቲና የበኩሏን ድጋፍ እንድታደርግም ጥሪ አቅርበዋል።
በፋርማሲዮቲካል ዘርፍም አርጀንቲና ሰፊ ልምድ ያላት በመሆኑ በቀጣይ አርጀንቲናውያን ባለሀብቶች ፋሲሊቲ በተሟላላቸው የኢንዱስትሪ ፓርኮች በመግባት ኢንቨስት እንዲያደርጉም የደቡብ አሜሪካና የካሪቢያን ፓርላማ ወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢው ጥሪ አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ ለዓለም የንግድ ድርጀት አባልነት ጥረት እያደረገችና ሲሆን የአርጀንቲና ድጋፍ እንዳልተለያትም ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ የአርጀንቲና አምባሳደር ጁዋን ኢግናሲዮ ሮካታግሊታ በበኩላቸው፤ አርጀንቲና ከኢትዮጵያ ጋር በትምህርት፣ በስፖርት፣ በንግድ እና በግብርና ዘርፎች በጋራ እየሰራች መሆኑን ጠቁመው፣ በቀጣይም ይህንኑ በይበልጥ አጠናክራ የምትቀጥል መሆኗን ማረጋገጧን አዲስ ማለዳ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያገኜችው መረጃ ያመላክታል።
አዲስ_ማለዳ
