የጸረ ጾታዊ ጥቃት ቀንን ለማክበር እንደ ሀገር በተያዘው ሀገራዊ ንቅናቄ መሰረት ክልሎችም ከዛሬ ህዳር 16 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የግንዛቤ ማስጨበጫና የድጋፍ ስራ እንደሚያከናውኑ ለጣቢያችን ገልጸዋል።
በትግራይ ክልል ዘመቻውን ለሚሊዮኖች ለማከናወን መታቀዱንና በርካታ የጥቃት ሂደቶችና ስጋቶችም በክልሉ መኖራቸውን በትግራይ ክልል የሴቶች ጉዳይ ቢሮ ምክትል ሃላፊና የጀንደር ክፍል ዳይሬክተር ወ/ሮ አለማት አማረ ለጣቢያችን ገልጸዋል።
በክልሉ አሁን ላይ 152ሺሕ ያህል ድጋፍ የሚፈልጉ ሴቶች መኖራቸውን የተናገሩት ምክትል ሃላፊዋ ፤ይህ ቁጥር ከሰሜኑ ጦርነት ጀምሮ የነበረ ጥናት ውጤት መሆኑንም ገልጸዋል።
152ሺው ድጋፍ ከሚፈለግ ሴቶች ውስጥ ጾታዊ ጥቃት ከፍ ያለውን ድርሻ ይይዛል ሲሉም ምክትል ሃላፊዋ ተናግረዋል። ዛሬም በክልሉ ሴቶችና ህጻናት አስቸጋሪ ሁኔታን እያሳለፉ እንደሚገኙና ለዚህም ከፍተኛ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል።
ከ2014 ዓ.ም እስካለፈው ጥቅምት ወር 2018 ዓ.ም ድረስ ባሉ ጥናቶች በትንሹ 22 ሴቶች በጾታዊ ጥቃት ምክንያት ህይወታቸዉ ማለፉ እንዲሁም 73 ያህል ሴቶችና ህጻናትም የመደፈር ወንጀል እንደተፈጸመባቸዉ ምክትል ሃላፊዋ ተናግረዋል።
ለ9.5 ሚሊዮን ያህል ማህበረሰብ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራ ለመስራት ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን የገለጹት በአማራ ክልል ሴቶች፣ ህጻናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ የሴቶች ንቅናቄ ተሳትፎ ዳይሬክተር ወ/ሮ ደስታ ፈንታ ናቸው።
በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች ንቅናቄውን ከአዳራሽ ውጭ ለማከናወን ማቀዳቸውን የገለጹት ዳይሬክተሯ በክልሉ ባለው ግጭት ምክንያት ጾታዊ ጥቃት መባባሱንና በጥናት ድጋፍ የሚፈልጉትን በመለየት ሂደት ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ዛሬም ለጾታዊ ጥቃት መባባስ የግንዛቤ ክፍተት እንዳለ ሆኖ የፍትህ አካላት በቂ ምላሽ አለመስጠት ግን ሌላኛው አባባሽ ምክንያት ነው ብለዋል።
ጾታዊ ጥቃት መከላከል የሚቻለው በማህበረሰቡ እገዛና በፍትህ አካላትም በቂ ምላሽ ነው ሲሉ ክልሎቹ አስታውቀዋል።
(መናኸሪያ ሬዲዮ)
